በተቃዋሚ ፓርቲ ወጣት አባላት ላይ የሚወሰደው እርምጃ አስከፊ ሆኖ ቀጥሏል


ሚያዝያ ፲፪ (አስራ ሁለት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ገዢው ፓርቲ ከመጪው ምርጫ ጋር በተያያዘ ህዝቡን አስተባብረው ህዝባዊ አመጽ ያስነሱ ይሆናል በሚል የሚጠረጥራቸውን ወጣቶች ሁሉ እያፈሰ ከማሰር አልፎ ፣ አንዳንዶች እየተገደሉ ሌሎች ደግሞ አሰቃቂ ድብደባ እየተፈጸመባቸው ነው።
በባህርዳር ዩኒቨርስቲ ዋናው ግቢ የሚማር አንድ የመድረክ አባል እንደሆነ የሚታወቅ የ3ኛ አመት ተማሪ ግቢው ውስጥ ወድቆ ከተገኘ በሁዋላ የተሻለ ህክምና ለማግኘት ባለመቻሉ ህይወቱ አልፎአል።
በቴክስታይል የትምህርት ክፍል የኢንጀሪንግ 3ኛ አመት ተማሪ የነበረው ያዕቆብ ቡዴ ከደቡብ ህዝቦች ክልል የመጣ ሲሆን ሰኞ ግንቦት 10/2007 ዓ.ም ከምሽቱ በ5 ሰዓት በግቢው ውስጥ ወድቆ በመገኘቱ በአካባቢው ሲዘዋወሩ የነበሩ ተማሪዎች አግኝተውት ፣ በዩኒቨርስቲው ክሊኒክ እንዲረዳ ቢያደርጉትም ወደ ተሻለ ህክምና ሊወሰድ ባለመቻሉ ህይወቱ ከሌሊቱ 8 ሰዓት ማለፉን የዩኒቨርስቲው ምንጮች ገልጸዋል፡፡
ተማሪ ያዕቆብ ቡዴ የመድረክ ፖለቲካ ፓርቲ ደጋፊ ሆኖ እንደሚንቀሳቀስ በቅርብ የሚያውቁት ተማሪዎች ይናገራሉ፡፡ የገዢው መንግስት ካድሬዎች በየጊዜው ይዝቱበት እንደነበር የሚናገሩት የልጁ ጓደኞች በዩኒቨርስቲ ቆይታው አንድም ቀን ታሞ እንደማያውቅ ያክላሉ። ወጣቱ በልብ ህመም እንደሞተ ተደርጎ የሚሰጠው መግለጫ ትክክል አለመሆኑን የሟቹ ጓደኞች ገልጸዋል።
የባህርዳሩ ፈለገ ህይወት ሪፈራል ሆስፒታል በሚገኝበት ከተማ እና በርካታ አምቡላንስና የዩኒቨርስቲው መኪኖች እያሉ ወደ ህክምና ማድረስ ሲቻል በዩኒቨርስቲው አነስተኛ ክሊኒክ በቂ እርዳታ ሳደረግለት ህይወቱ በማለፉ ከፍተኛ ንዴት ውስጥ የሚገኙት የሟች ጓደኞችና የትምህርት ክፍል አጋሮቹ ፣ ጓደኛችን ሆን ተብሎ እንዲሞት ተደርጓል በማለት ብስጫታቸውን እየገለጹ ነው።
የሟች አስክሬን ከሌሊቱ በ10 ሰዓት በዩኒቨርስቲው መኪና ተጭኖ በድብቅ ወደ ትውልድ ሀገሩ ሸኖ ከተማ መላኩን የውስጥ ምንጮች ገልጸዋል፡፡
ከአሁን በፊት በዩኒቨርስቲው ውስጥ የሚማሩ ተማሪዎች በህመምም ሆነ በተለያዩ ምክንቶች ሲያርፉ ተማሪውና የዩንቨርስቲው ማህበረሰብ በነቂስ ወጥቶ በዲፓርትመንቱ የአበባ ጉንጉን ተዘጋጅቶ እንደሚሸኝ የሚገልጹት ተማሪዎች፣ የተማሪው አስከሬን በድብቅ አንዲሄድ መደረጉ ከአሟሟቱ ጋር በተያያዘ ሌሎች ችግሮች እንዳይነሱ በመስጋት ነው ይላሉ።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የሰማያዊ ፓርቲ አባል የሆነው አቤል ኤፍሬም በደረሠበት ድብደባ ኩላሊቱ ተጎድቶ ምንሊክ ሆስፒታል መግባቱ ታውቋል።
ወጣት አቤል በደህንነቶች ተይዞ ወደማዕከላዊ መወሰዱን የገለጹት የቅርብ ጓደኞቹ፤ ማዕከላዊ እስር ቤት ከቀኑ 5 ሠዓት ጀምሮ እስከ እኩለ-ሌሊት በተፈፀመበት ከፍተኛ ድብደባ ኩላሊቱ በመጎዳቱ ሌሊት 11 ሠዓት ላይ ወደምኒልክ ሆስፒታል እንደተወሰደ ተናግረዋል።
እንደ ትግል ጓደኞቹ ገለጻ አቤል ከመያዙ ከአንድ ቀን ቀደም ብሎ በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ በሚገኙ የመንግስት ትምህርት ቤቶች ውስጥ በማስተማር ላይ የሚገኙ 13 መምህራን በፖሊስ ተይዘው የታሰሩ ሲሆን፤ አቤል ማዕከላዊ በገባበት ቀን ፦” በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ የሚገኙ መምህራንን በህቡዕ እንደምታደራጅ ደርሰንበታል” የሚል ክስ ቀርቦበታል።
ለመርማሪዎቹ ስለጉዳዩ ምንም የሚያውቀው ነገር እንደሌለ የገለፀው ወጣት አቤል፤ ብሔሩን ሲጠየቅ “ብሔሬ ኢትዮጵያዊ ነው” ማለቱ ያናደዳቸው የደህንነት ኃይሎች መታወቂያውን በመቀበል ብሔሩን ለማጣራት ሲሞክሩ ብሔር የሚለው ስፍራ ላይ ምንም ብሄር አለመጠቀሱን ተመልክተዋል።
“ተያዥ” በሚለው ስፍራ ላይ ታማኝ በየነ የሚል ፅሁፍ በማገኘቱ፤ በብስጭትና በእልህ እየተፈራረቁ ክፉኛ እንደደበደቡት ጓደኞቹ ይገልጻሉ።
ሌሊቱን በሙሉ ምግብ እና ውሃ ሳይቀምስ ክፉኛ ሲደበድቡት ያደሩት የደህንነት ሀይሎች ፤ ሌሊት ላይ የአቤልን መድከም ሲረዱ ምኒልክ ሆስፒታል እንደወሰዱት ገልጸዋል።
በምኒልክ ሆስፒታል የነበሩ የ ዐይን ምስክሮች አቤል ሆስፒታል ሲደርስ በድብደባ ብዛት ኩላሊቲ እንዳበጠ እና የለበሰው ልብስ ከጥቅም ውጪ እንደሆነ መናገራቸውን ጓደኞቹ ተናግረዋል።
ነገረ ኢትዮጵያ ባወጣው ዘገባ ደግሞ ቤተሰቦቹ ምኒልክ ሆስፒታል ለመጠየቅ በሄዱበት ወቅት ዶክተሮቹ አቤልን መጠየቅ እንደማይቻል ገልጸውላቸዋል።
አቤል ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰበትና ማንንም ማናገር እንደማይችል ሆስፒታሉ ውስጥ ከሚሰሩ ሰዎች መረጃ ማግኘታቸውን ቤተሰቦቹ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡
አቤል ሰማያዊ በጠራው አንድ የተቃውሞ ሰልፍ ላይ በከፍተኛ ሁኔታ ተደብድቦ ራሱን ስቶ ከሞት መትረፉ በወቅቱ መዘገቡ ይታወቃል። አቤል ኤፍሬም ታህሳስ ወር ላይ ከኢሳት ጋር ባደረገው ቃለምልልስ አንድ ሃይለ ሃለፎም የሚባል ፖሊስ ብሄርህ የት ነው ብሎ ሲጠይቀው ኢትዮጵያዊ ብሎ መመለሱን፣ ከዚያም ጥያቄ ሲበዛበት አባቴ የተወለደው አድዋ ነው ብሎመናገሩን፣ ፖሊሱም ” እና አንተ ደግሞ ምን ጎድሎብህ ነው የምትታገለው” ብሎ ከመለሰለት በሁዋላ ስርአቱን አምርሮ እንዲታገለው እንዳደረገው” ገልጾ ነበር ።
በአዲስ አበባ የ22 ማዞሪያ ሰፈር ነዋሪ የኾነው የ25 ዓመቱ ወጣት ሢሳይ ተሾመ በእስር ቤት ውስጥ በደረሰበት አስከፊና ተደጋጋሚ ድብደባ ከጥቂት ቀናት በፊት ለህልፈተ ህይወት እንደተዳረገ መዘገባችን ይታወሳል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የቀዳሚ ገፅ ጋዜጣ ሥራ አስኪያጅና አምደኛ እንዲሁም የሚሊዮኖች ድምፅ ጋዜጣ ሪፖርተር የነበረው ሀብታሙ ምናለ ዛሬ ከረፋዱ 5፡30 ላይ ቦሌ ሩዋንዳ ከሚገኘው መኖሪያ ቤቱ በፖሊሶች ተይዞ በአካባቢው ወደ ሚገኘው ፖሊስ ጣቢያ መወሰዱ ታውቋል።
እስካሁን በሚደርሱን መረጃዎች በአለፉት 2 ወራት ከ4 ሺ በላይ ወጣቶች በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ተይዘው ታስረዋል። ከ3 ሺ ያላነሱ ወጣቶች አዋሽ አርባ አካባቢ ከሚገኝ የገጠር እስር ቤት ውስጥ ሲገኙ፣ ንቁ የተቃዋሚ አባላት ናቸው የተባሉት ደግሞ በአዲስ አበባና በክልሎች ታስረው ይገኛሉ።
ገዢው ፓርቲ በክልሎችና በአዲስ አበባ ያለውን ደህንነቱን እያጠናከረ ሲሆን፣ በአንዳንድ ከተሞች በከፍተኛ ሁኔታ የታጠቁ ወታደሮች በህዝቡ ላይ የስነ ልቦና ጫና እያሳደሩ ነው።

No comments:

| Copyright © 2013 Lomiy Blog