የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በIMF እይታ

የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ኣስመልክቶ ላለፉት 9 እና 10 ዓመታት በተለይ ከመንግስት በኩል የሚሰማው እጥፍ ድርብ እድገት ወይንም በእንግሊዝኛው Double digit grorth ያውም ከ 11 በመቶ ያላነሰ ወይንም ከዚያ በላይ መሆኑ ይታወቃል። ተቃዋሚዎች በዚያች ኣገር ያንን ያህል እድገት ያውም በኢህኣዲግ የእጅ ኣዙር እዝ ኢኮኖሚ የማይታሰብ ነው እያሉ

ማጣጣላቸው ባይቀርም የዓለም ባንክ እና ዓለም ዓቀፉ የገንዘብ ተቐም IMF ግን ሙሉ በሙሉም ባይሆን የመንግስትን የዕድገት ብስራት የሚጋሩት ይመስላል። የመንግስት ባለስልጣናት ለተባለው እድገት በየዘርፉ እና በየአካባቢው እየተገነቡ ያሉ የመሰረተ ልማት ኣውታሮቶችን እና የዜጎች የነፍስ ወከፍ ገቢ መሻሻሉን እንደ ማስረጃ ሲያቀርቡ ተቃዋሚዎች እና ኣንዳንድ ገለልተኛ የሆኑ ባለሙያዎችም እንዲሁ ከወረቀት ኣልፉ መሬት ላይ ያረፈ እና የህብረተሰቡን ኑሮ የቀየረ እድገት ኣላታየም ሲሉ በተቃራኒው ይከራከራሉ። የዓለም ባንክ እና ዓለም ዓቀፉ የገንዘብ ተቐም IMF በበኩላቸው በኢትዮጵያ መጋነኑ ባይቀርም ነገር ግን ፈጣን እድገት መኖሩን እና በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ደግሞ የህዝቡ ኑሮም እየተቀየረ መሆኑን ይመሰክራሉ።
የተለመደው የኢኮኖሚ እድገት መለኪያ ባለሙያዎችም እንሚሉት ኣጠቃላይ የኣገር ውስጥ ገቢ እና ምርት ዕድገት ሲሆን የኢትዮጵያ መንግስትም በአብዛኛው በዓማካኝ 11 በመቶ ለተባለው ዓመታዊ ዕድገት ዋንኛ መሰረቱ የግብርና ምርት እድገት መሆኑን ሲገልጽ ቆይቷል። ይሁን እንጂ የውጪው እርዳታ እና ብድር ግብዓቶችም ሆኑ የውጪ ምንዛሬውም የሚኖራቸው ድርሻ ቀላል ኣለመሆኑን መገመት ይቻላል።
የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ እድገት በሚመጣውም ዓመት በተመሳሳይ መልኩ ሊቀጥል እንደሚችል የገመተው ዓለም ዓቀፉ የገንዘብ ተቐም IMF ባለፈው ወር ይፋ ባደረገው ዓመታዊ ሪፖቱ ይህንኑ ጠቁሟል። መንግስታዊ ለሆኑ የልማት ተቐማት የሚደረገው የገንዘብ ድጋፍ ክፍተት ካሳየ እና የውጪ ምንዛሪ እጥረት ካጋጠመ ግን የተባለው እድገት ላይሳካ እንደሚችል IMF ኣልሸሸገም።
በቀጣዮቹ 12 ወራት የኣገሪቱ ኣጠቃላይ የኣገር ውስጥ ምርት በዓማካኝ የ 7 በመቶ እድገት ይኖረዋል የሚለው IMF ይህ ግን የፖሊሲ ማስተካከያ ካልታከለበት ኣንድ ቦታ ላይ መቆሙ ኣይቀሬ ነው ሲልም ያስጠነቅቃል።
መንግስት መር የኢኮኖሚ ልማት ፖሊሲን የሚከተለው የኢትዮጵያ መንግስት ይላል IMF እንደ ዓባይ ግድብ የመሳሰሉ ግዙፍ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶችን በራሱ ዓቅም ለማካሄድ ወስኖ ጀምሮታል። ይህ ፕሮጀክት የ 80 ቢሊዮን የኢትዮጵያ ብር ወጪ የሚጠይቅ ሲሆን በሪፖርቱ መሰረት 10 በመቶ የሚሆነውን የኣገሪቱን ዓመታዊ የኣገር ውስጥ ገቢ መጠን ይወስዳል ማለት ነው። እናም እድገቱ በዚህ ምክኒያት እንዳይሰናከል እና ቀጣይነት እንዲኖረው ለማድረግ ከተፈለገ መንግስት የግል ባለሀብቶች በላቀ ደረጃ በኢንቨስትመንቱ ውስጥ እንዲሳተፉ በር ሊከፍትላቸው ይገባል ሲል IMF ይመክራል።
የኣገር ውስጡ የልማት እንቅስቃሴ ከፍተኛ የኢንቨስትመንት ግብዓትን ይጠይቃል። የገንዘብ ኣቅርቦቱ ግን መሰናክል የሞላበት ነው ሲልም IMF ይወቅሳል። ለዓብነት ያህልም የግል ባንኮች እንቅስቃሴ ኣለመበረታታቱ እና የመnንግስት ባንኮችም ቢሆኑ ለግሉ ዘርፍ የሚሰጡት ብድር በቂ ኣለመሆኑን IMF ይጠቅሳል። ያለ ግል ባለ ሀብቶች ንቁ ተሳትፎ ግን የተጀመረው የኢኮኖሚ እድገት ቀጣይ ሊሆን እንደማይችል ሊሰመርበት ይገባል ሲል ሪፖርቱ ይቀጥላል።
የሆነ ሆኖ ይላል ዘገባው እ ኣ ዘ ኣ ከ 2001 እና 2002 ጀምሮ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በዓማካኝ በዓመት በ 7 በመቶ እድገት ኣሳይቷል። ይህም ይላል ዘገባው በዚያች ኣገር የድህነት እርከኑን በግማሽ ቀንሶታል። ይህ ማለት በሪፖርቱ መሰረት በ 2005 60,5 የነበረው የድህነት እርከን በ 2012 ወደ 30,7 ወርዷል። ይህም የበርካቶችን ኑሮ ኣሻሽሎታል የስራ ኣጥ ቁጥርንም በእጅጉ ቀንሶታል ያለው IMF በዚህ መካከል ግን የመንግስት በተለይም የገዢው ፓርቲ ኩባንያዎች በኣገር ውስጥ የገንዘብ ኣቅርቦት ተጠቃሚ ሲሆኑ የግል ተበሪዎች ግን ገለል መደረጋቸውን ሳይጠቅስ ኣላለፈም።
2012/13 7 በመቶ የተመዘገበው እድገት በዋናነት ከግብርና ከኮንስትራክሺን እና የኣገልግሎት ዘርፎች የተገኘ መሆኑን የጠቀሰው IMF ከዚሁ የተነሳ በ 2011 40 በመቶ ደርሶ የነበረው የዋጋ ግሽበትም በ 7 በመቶ መቀነሱን ጠቅሶ ነገር ግን በ 2012 2,8 ቢሊዮን የነበረው የበጀት እጥረት በ2013 ወደ 3 ቢሊዮን ከፍ ማለቱንም በሪፒርቱ ኣመልክቷል።

በኣፍሪካ ዋናዋ የቡና ኣምራች የሆነችው ኢትዮጵያ የብድር እና እዳ ይዞታዋን በሰከነ መልኩ ለማስኬድ ያስችላት ዘንድ IMF እንደሚለው የፋይናንስ ስርዓቷን ማሻሻል ይኖርባታል። በተለይ የግል ባንኮች በብድር ባሰራጩት ገንዘብ መጠን 27 በመቶ ያህል የመንግስት ሰነድ ሽያጭ እንዲገዙ የሚያስገድደውን ደንቃራ ደንብ ማስወገድ እንደሚኖርባት ኣመልክቷል።
ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ለዓመታት ያህል በስሌቱ ላይ ስምምነት ኣልነበረንም የሚሉት በአዲስ ኣበባ የIMF ተጠሪ ሚ/ር ጃን ሚኬልሰን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ መንግስት መጠነኛ ማሻሻያ ማድረጉን ይናገራሉ።
የኢኮኖሚ ባለሙያው እና በኢትዮጵያ ፓርላማ ብቸኛው የተቃዋሚ ፓርቲ ተወካይ የሆኑት አቶ ግርማ ሰይፉ ግን የ IMF ዘገባ በመንግስት መረጃዎች ላይ የተመሰረተ በመሆኑ ችግር ያለበት ነው ይላሉ።
መረጃዎችን ከመንግስት እንደሚቀበሉ ያልሸሸጉት የ IMF ተወካይ ሚ/ር ጃን ሚኬልሰን ነገር ግን በራሳችን ስልት እንመዝናቿለን ይላሉ።
የኣንድነት ለዲሞክራሲ እና ለፍትህ ፓርቲ ም/ሊቀመንበሩ አቶ ግርማ ሰይፉ በበኩላቸው የIMF መመዘኛ በተዛቡ የመንግስት መረጃዎች ላይ እስከተመሰረተ ድረስ ትርጉም ኣይኖረውም ሲሉ በደርግ ጊዜ የታዘቡትን ተመሳሳይ የእድገት መለኪያ ያስታውሳሉ።ምንም እንኩዋን መንግስት በሚያስተዋውቀው ደረጃ ባይሆንም የተጠቀሰው እድገት ህብረተሰቡን በስፋት እየጠቀመ መሆኑን IMF ያምናል ይላሉ ሚ/ር ሚኬልሰን
አቶ ግርማ ሰይፉ ግን ይህንን ኣይቀበሉትም በኣጠቃላይ ግን የኢትዮጵያ መንግስት ኣንድ ነገር ካላደረገ በስተቀር የኣገሪቱ እድገት ኣሁን ኣንድ ሊያልፈው ከማይችል ፈታኝ ደረጃ ላይ ደርሷል ይላሉ በአዲስ ኣበባ የIMF ተጠሪ ሚ/ር ጃን ሚኬልሰን።
ጃፈር ዓሊ
አርያም ተክሌ
Source: www.dw.de

No comments:

| Copyright © 2013 Lomiy Blog