የኢራን ሥምምነትና ዉዝግብ

ኢራን ድብቅ የኑክሌር ተቋም እንዳለት ከታወቀበት ከሁለት ሺሕ ሁለት ጀምሮ በቴሕራንና በምዕራባዉያን ሐገራት ፖለቲከኞችን መካከል የደራዉ ዉዝግብ ለመጀመሪያ ጊዜ-አንድ እልባት አግኝቷል። የእስራኤል-ምዕራባዉያን ልዩነት፥ የኢራን-እስራኤል ዉዝግብስ ነዉ?-የዛሬዉ ጥያቄ 
የአያቶላሕ ሩሑላሕ ሆሚኒዋ «ታላቅ ሠይጣን» የድብቅ ዲፕሎማቶች፥ ከጆርጅ ዳብሊዉ ቡሿ «የሰይጣን ዛቢያ» ስዉር መልዕክተኞች ጋር በዓለም የፖለቲካ መድረክ ብዙም በማትታወቀዉ ሐገር፥ በድብቅ ሆቴል፥ በዘወርዋራ አሳንስር ወይም ሊፍት ዉስጥ የጀመሩት ድርድር ቅዳሜ-ለዕሁድ አጥቢያ በይፋ ዉል ተቋጠረ።ዤኔቭ።
«ከከባድ ድርድር በሕዋላ ለረጅም ጊዜ፥ አጠቃላይ መፍትሔ በሚያደርሰን የጋራ የድርጊት መረሐ-ግብር ላይ ዛሬ ተስማምተናል።»
የአዉሮጳ ሕብረት የዉጪ ግንኙነት ሐላፊ ወይዘሮ ካትሪን አሽተን።የድብቅ፥ ይፋዉ ድርድር ሒደት፥ የስምምነቱ ይዘት፥ የተቃዉሞዉ እንዴትነት ያፍታ ዝግጅታችን ትኩረት ነዉ።አብራችሁኝ ቆዩ።

ፕሬዝዳንት ባራክ ኦቦማ በ2009 (ዘመኑ በሙሉ እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር ነዉ) የፕሬዝዳንትነቱን ሥልጣን ሲይዙ በተለይ በዉጪዉ መርሕ ሊፈፅሙት ከገቡት ቃል ብዙዉ እያቃታቸዉ፥ ሌላዉ እየከዳቸዉ፥ ወይም አያሟለጫቸዉ መምጣቱን ሲገነዘቡ ለቃል-እምነታቸዉ ገቢራዊነት «ስስ ብልት» የሚባል አይነት ሲያፈላልጉ-ኢራንን አገኙ።ኦባማ የዲፕሎማሲዉን ስስ ብልት ሲያማትሩ የኢራን አያቶላሆች በሐገራቸዉ ላይ የተጣለዉ ተደጋጋሚ ማዕቀብ፥ የሐገሪቱን ምጣኔ ሐብት እያደቀቀ፥ የሕዝቡን ምሬት እያናረ ያገዛዝ ሐይል ጉልበታቸዉን እየተፈታተነ መምጣቱን በቅጡ ተገንዝበዉታል።
ከ1979 (ዘመኑ በሙሉ እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር ነዉ) የኢራን እስላማዊ አብዮት ወዲሕ በጠላትነት የሚፈላለጉ፥ በሰይጣንነት የሚወጋገዙ፥ በተዘዋዋሪ የሚቆራቆሱት ሐገራት መሪዎች የጥላቻ-ዉርቁሳቸዉ ክረት ጨርሶ ከመበጠሱ በፊት ለየራሳቸዉ መላ ሲሹ-ተገናኙ።ቅዳሜ-ለዕሁድ አጥቢያ በአሜሪካኖቹ በኩል ዉል ፈራሚዉ ጆን ኬሪ ናቸዉ።ምናልባት ካስወቀሰ፥ ተወቃሽ ተመስጋኙ፥ ፕሬዝዳት ባራክ ኦቦማ ናቸዉ።
«ዛሬ፥ ዩናይትድ ስቴትስ ከቅርብ ወዳጆቻችን እና ተሻራኪዎቻችን ጋር ሆነን የኢራን እስላማዊት ሪፐብሊክ የኑክሌር መርሐ-ግብር የፈጠረብንን ሥጋት ለማስወገድ ከአጠቃላይ መፍትሔ ለመድረስ የሚረዳ የመጀመሪያ እርምጃ ወስደናል።ሥልጣን ከያስኩበት ጊዜ ጀምሮ ኢራን የኑክሌር ጦር መሳሪያ እንዳይኖራት ለማገድ ያለኝን ቁርጠኝነት ግልፅ አድርጌያለሁ።ብዙ ጊዜ እንዳልኩት ይሕን ጉዳይ ለማስወገድ ጠንካራ ምርጫዬ ሰላማዊ መንገድ ነዉ።እና የዲፕሎማሲ እጃችንን ዘርግተናል።»
«የዲፕሎማሲ እጅ» የተዘረጋዉ በማይታወቁት ዲፕሎማቶች፥ በዓለም የፖለቲካ መድረክ ስሟ በማይጠራዉ ሐገር በኩል ነበር።መጋቢት-ሁለት ሺሕ አስራ-ሰወስት።ሙስካት-ኦማን ጦር ሠፈር ያረፈዉ የአሜሪካ የጦር አዉሮላን ያሳፈራቸዉ ሠዎች ያዉ እንደተለመደዉ የአሜሪካ የጦር መኮንኖች ወይም ረዳቶቻቸዉ እንጂ የአሜሪካ ትላልቅ ዲፕሎማቶች መሆናቸዉን ያወቀ-የጠረጠረ፥ ዓላማቸዉን የገመተም ታዛቢ-ጋዜጠኛ አልነበረም።
ቀለል ያለ ልብስ፥ ጠቆር ያለ መነፅር አጥልቀዉ ከጦር አዉሮፕላኑ፥ በጥቋቁር መስታዎቶች ከተጋረዱት መኪኖች ከተጋቡት አሜሪካዉያን ቢንስ ሁለቱ የዩናይትድ ስቴትስ ምክትል የዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ዉልያም በርንስ እና የምክትል ፕሬዝዳት ጆ ባይደን ብሔራዊ የፀጥታ አማካሪ ጃክ ሰሊቫን ነበሩ።የተቀሩት የቴክኒክ አማካሪዎች።
በኢራን በኩል የጄኔቩ ዉል እንዲፈረም አዛዡ ልዕለ መሪ አያቶላሕ ዓሊ ኻሚኒ፥ ሥልት ቀያሹ ፕሬዝዳት ሐሰን ሩሐኒ፥ ዉል ፈራሚዉ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር መሐመድ ሳሪፊ ናቸዉ።
«እኛ ሁላችንም የማያስፈለግ ቀዉስ የሚወገድበትን አጋጣሚ መመልከቱ ጠቃሚ ነዉ ብዬ አምናለሁ።እና የኢራን ሕዝብ መብትን በማክበርና ኢራን ፍፁም ሠላማዊ ለሆነ አገልግሎት በምታዉለዉ የኑክሌር መርሐ-ግብር ላይ ጥርጣሬን በማስወገድ ላይ ተመሠረተ አዲስ አድማስ መክፈቱ (ጠቃሚ) ነዉ።
እንደገና መጋቢት፥-የትልቂቱ ሐገር ትላልቅ ዲፕሎማቶች እንደ ጦር መኮንን በጦር አዉሮፕላን ተጭነዉ በዘመኑ ዓለም የፖለቲካ መድረክ ብዙም ከማትታወቀዉ ሐገር ከመግባታቸዉ በፊት፥ «በተራ» የመንገደኞች አዉሮፕላን ተሳፍረዉ ሙስካት የገቡትን ሠዎች ያየ-ያስተዋላቸዉ ከነበረ፥ አንድም የፋርስ ቱጃር ነጋዴዎች አለያም አስተማሪ፥ ወይም ጠበቆች እንጂ የእስላማዊቷ ሪፐብሊክ ልዩ መልዕክተኞች ናቸዉ ብሎ መጠርጠሩ ሲበዛ አጠራጣሪ ነበር።

የሁለቱ ሐገራት ዲፕሎማቶች እና የቴክኒክ ባለሙያዎች ከማጋቢት ጀምሮ ቢያንስ ስድስት ጊዜ ሙስካት ዉስጥ በድብቅ ተደራድረዋል።ተደራዳሪዎች የታዛቢ ትኩረትን በተለይ የጋዜጠኞችን አይን፥ ጆሮ ላለ መሳብ ሆቴል ክፍሎች፥ አሳንስር-ወይም ሊፍት ዉስጥ ተደብቀዉ እስከ መነጋገር ደርሰዋል።ከስድስት ወራት በፊት በድብቅ የተጀመረዉ ድርድር ከዕሁድ አጥቢያዉ ስምምነት መድረሱ ፕሬዝዳት ባራክ ኦባማ እንዳሉት ለዓለም ሠላም ጠቃሚ ነዉ።#

«ዛሬ፥ ዲፕሎማሲ፥ ዓለም ይበልጥ አስተማማኝ የምትሆንበትን አዲስ ጎዳና ከፍቷል፥ ለወደፊቱ የኢራን የኑክሌር መርሐ ግብር ለሠላማዊ አገልግሎት የሚዉል መሆኑን፥ የኑክሌር ጦር መሳሪያ እንደማትሠራ የምናረጋግጥበትን (ሥልት) ከፍቷል።የዛሬዉ ዉል የመጀመሪያዉ ደረጃ ቢሆንም፥ ታላቅ እመርታ ነዉ።»
ለኢራን ታዳላለች ተብላ የምትጠረጠረዉ ሩሲያም፥ የሐገሪቱ ፕሬዝዳት ቭላድሚር ፑቲን እንዳሉት ስምምነቱ ለዓለም ሠላም ከመጥቀሙ ባለፍ ዉዝግብ፥ ግጭት፥ አለመግባባትን በድርድር መፍታት እንደሚቻል ጥሩ አብነት ነዉ።የቻይና ዉጪ ጉዳይ ሚንስቴር መስሪያ ቤት ባወጣዉ መግለጫዉም ጄኔቭ ላይ የተፈረዉ ዉል ይበልጥ ፍሬያማ እንዲሆን ድርድር ዉይይቱ በተጀበረበት መንፈስ መቀጠል አለበት።
ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ የዩናይትድ ስቴትስ የቅርብ ወዳጆች ያሏቸዉ የብሪታንያና የፈረንሳይ ባለ ሥልጣናትም ስምምነቱን አድንቀዋል።በፀጥታዉ ጥበቃ ምክር ቤት ዉስጥ ድምፅን በድምፅ የመሻር ሥልጣን ባይኖራትም በአሜሪካ ወዳጅነቷ፥ በምጣኔ ሐብት አቅሟም በድርድሩ፥ የድርድሩን ዉጤት በፊርማ በማፅደቁም የተካፈለችዉ ጀርመንም የሐገሪቱ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ጊዶ ቬስተር ቬለ እንዳሉት ስምምነቱ ኢራን የኑክሌር ቦምብ እንዳትታጠቅ ለማከላከል የሚደረገዉ ጥረት ዲፕሎማሲያዊ ዉጤት ነዉ።
«አንድ ግብ አለን።ኢራን የኑክሌር ጦር መሳሪያ እንዳትታጠቅ ማገድ።ከዚያ ግባችን ለመድረስ በዤኔቩ ሥምምነት አንድ ጠቀም ያለ እርምጃ ወደፊት ተራምደናል።ከግባችን በፖለቲካዊና ዲፕሎማሲያዊ መንገድ ለመድረስ እንፈለግለን፥ ባካባቢዉ ዉጥረት እንዳይባባስ በየትኛዉም መንገድ መታገድ አለበትና።»

ስምምነቱ ለስድስት ወር የሚፀና ነዉ።በዚሕ ስድስት ወራት ኢራን ዩራኒየም የማብላላት ወይም የማንጠር ሥራዋን ወደ ሃያ-በመቶ ዝቅ ታደርጋለች።የኑክር ተቋማቷን የዓለም አቀፉ የአዉቶሚክ ሐይል ተቆጣጠሪ ባለሥልጣን (IAEA) ባለሙያዎች እንዲፈትሹ ክፍት ታደርጋለች።
ለኢራን ባንፃሩ በተከታታይ ከተጣለባት ማዕቀብ በመኪና ኢንዱስትሪዎችዋ፥ በጌጣጌጥ ወይም በዉድ ማዕድናት፥ ከዉጪ ሐገር ባላት የገንዘብ ልዉዉጥ እና ከነዳጅ ዘይት ተዋፅኦ በጣም በጥቂቱ ላይ የተጣለዉ ገደብ ይነሳላታል።በጥቅሉ ሚቀጥሉት ስድስት ወራት ኢራን ሰባት ቢሊዮን ዶላር ያክል ማስገባት ትችላለች።
የኢራን የኑክሌር ተቋማት የሚያብላሉት ወይም የሚያነጥሩት ዩራኒየም ወይም የፑሉቱኒየም መጠን በሃያ በመቶ ከተገታ ባለሙያዎች እንደመሠከሩት እስላማዊቷ ሪፐብሊክ «የሚፈራዉን» የኑክሌር ቦምብ ማምረት አትችልም።የጀርመኑ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር «ዉጥረት እንዳይባባስ» ያሉለት ያ-አካባቢ ግን ከስምምነቱ በፊት እንደነበረዉ ሁሉ ከስምምነቱም በኋላም ከዉጥረት የመለየት ተስፋ አለማሳያቱ ነዉ-ዚቁ።
እርግጥ ከሁለተኛዉ የዓለም ጦርነት ፍፃሜ ጀምሮ ከዉጥረት ተለይቶ አያዉቅም።ዉጥረት በያማያጣዉ ምድር፥ ከዉጥረት፥ ግጭቱ ተዋኞች አንዷ-ከዩናይትድ ስቴትስ የቅርብ ወዳጆች ሁሉ ልዩ ወዳጅ፥ ከምዕራብ አዉሮጳዉያን ወዳጆች ሁሉ የወዳጆች ወዳጅ የሆነች አንዲት ሐገር አለች።እስራል።የኑክሌር ቦምብ መታጠቅዋ «የአደባባይ ሚስጥር» የሚባል አይነት ነዉ።
የዋሽግተን ብራስልስ ልዩ ወዳጆችዋ ለአካባቢዉ አይደለም ለዓለምም ሠላም ይጠቅማል በማለት ያንቆለጳጰሱትን ያሁንን ስምምነት እስራኤል አጣጥላ ነቅፋዋለች።እንዲያዉም የሐገሪቱ ጠቅላይ ሚንስትር ቢንያሚን ኔታንያሁ እንዳሉት ስምምነቱ «ታሪካዊ ስሕተት» ነዉ።
«ትናንት ማታ ጄኔቭ የተደረሰዉ፥ ታሪካዊ ስምምነት ሳይሆን ታሪካዊ ስሕተት ነዉ።ዛሬ ዓለም ይበልጥ አደገኛ ሥፍራ ሆኗል፥ ምክንያቱም በዓለም እጅግ አደገኛዉ ሥርዓት በዓለም እጅግ አደገኛዉን ጦር መሳሪያ ለማግኘት አንድ ከባድ እርምጃ ወስዷልና።የዓለም ትላልቅ ሐይላት፥ እራሳቸዉ ያስፀደቁትን የፀጥታዉ ጥበቃ ምክር ቤት ዉሳኔን ዘንግተዉ ኢራን ዩራንየም እንድታነጥር ተስማሙ።»

ኔታንያሁ ኢራን ዩራንየም እንድታነጥር ተፈቀደላት ባይ ናቸዉ።የአሜሪካዉ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ጆን ኬሪ ግን ኢራን ዩራንየም ማንጠር ትችላለች ያለዉ ማነዉ ባይ ናቸዉ።

«ይሕ የመጀመሪያዉ ደረጃ፥ ኢራን ዩራኒየም ማንጠር መብት አላት አይልም።እንደፈለገ እየተተረጎመ የፈለገዉ አስተያየት ቢሰጥም በዚሕ ሰነድ ዉስጥ፥ በአደገኛ ጦር መሳሪያዎች መከላከያ (ሕግ) በአራቱም መአዘናት መሠረት ዩራኒየም የማንጥር መብት (ለኢራን) የሚፈቅድ ነገር የለም።ሰነዱ አይፈቅድም።»
ስምምነቱ-ከስድስት ወር ባላይ አይፀናም።ያም ቢሆን በተለይ እስራኤልን እንደማያሰጋ ከፕሬዝዳት ኦባማ እስከ ጆን ኬሪ፥ ከፍራንሷ ኦላንድ እስከ ሎሯ ፋቢዮን፥ ከጊዶ ቬስተር ቬለ እስከ ዋንግ ዪ የሚገኙ የዓለም መሪ፥ ዲፕሎማቶች አረጋግጠዋል።ፕሬዝዳት ኦባማ በይፋ ከሰጡት ማረጋገጪያ ባለፍ ለእስራኤሉ ጠቅላይ ሚንስትር ሥልክ ደዉለዉ የስምምነቱን ይዘትና ዉጤት በግል አስረድተዋልም።
ኔታንያሁ ግን እስራል እራስዋን ለመከላከል መዘጋጀት አለባት በማለት ዝተዋል።በልዩ የፀጥታ አማካሪያቸዉ የሚመራ የመልዕክተኞች ቡድን ወደ ዋሽግተን እንደሚልኩም አስታዉቀዋል።ኢራን ድብቅ የኑክሌር ተቋም እንዳለት ከታወቀበት ከሁለት ሺሕ ሁለት ጀምሮ በቴሕራንና በምዕራባዉያን ሐገራት ፖለቲከኞችን መካከል የደራዉ ዉዝግብ ለመጀመሪያ ጊዜ-አንድ እልባት አግኝቷል። የእስራኤል-ምዕራባዉያን ልዩነት፥ የኢራን-እስራኤል ዉዝግብስ ነዉ?-የዛሬዉ ጥያቄ። ሥለ ማሕደረ ዜና ያላችሁን አስተያየት ወይም ማሕደረ ዜና ቢቃኘዉ ጥሩ ነዉ የምትሉትን ሐሳብ፥ በደብዴቤ፥ በስልክ፥ በፌስ ቡክ፥ በኤስ. ኤም ኤስ ና በኢሜይል አካፍሉን።ነጋሽ መሐመድ ነኝ ለዛሬ ይብቃን።
ነጋሽ መሐመድ
ሂሩት መለሰ
 Source: www.dw.de

No comments:

| Copyright © 2013 Lomiy Blog