ነገደ ኢትዮጵያ

ይህ ጽሑፍ መሪ ራስ አማን በላይ ‹የጥንቷ የኢትዮጵያ ትንሣኤ ታሪክ› በሚል ርዕስ ከመጽሐፈ ሱባኤ ተረጎምኩት ብለው በ1985 ዓ.ም. ካሳተሙት መጽሐፍ ከምዕራፍ ሦስት በሙሉ የተወሰደ ነው፡፡ ጽሑፍ እሳቸው እንዳዘጋጁት ነው እንጂ የተጨመረበት ወይም ኤዲት የተደረገ ነገር የለውም፡፡ መጽሐፉ በያዛቸው መረጃዎችም ሆነ በምንጩ በተለምዶ ከሚታወቀው የታሪክ መጽሐፎች ይለያል፤ ስለ መጽሐፉ ይዘት፣ ምንጭና አስፈላጊነት ብዙ ማለት ቢቻልም፤ መጽሐፉ ብዙ ሰዎች በቀላሉ አግኝተውት ያላለነበቡት በመሆኑ አንዱን ምዕራፍ ብቻ እንደነበረ እንደማሳያ ማቅረብ የተሻለ መስሎ ታይቶኛል፡፡ ለማንኛውም ስለ መጽሐፉ ሁኔታ ለማወቅ በመግቢያውና በመጽሐፉ ጀርባ ከጻፉት ላይ ቀንጭቦ ማየት ጠቀሜታ ይኖረዋልና እነሆ!
(ከመግቢያው የተወሰደ)
‹‹ይሄን የጥንቷ የኢትዮጵያ ታሪክ ሱዳን አጥባራ በነበርኩበት ጊዜ የኢትዮጵያ ታሪክ ከመጽሐፈ ሲራክ እያነበብኩ ስለ ድንጋይ ጥበብና ስለሌላም ስከታተል እንደቆየሁ ጀቢል ኩራርና ጀቢል ኦባ ወደሚባለው ሃገር ሄጄ የጥንት ቤተክርስቲያን ፍርስራሽና የክርስቲያን መቃብር አገኘሁ፤ ከዚያም ጀበል ኦባ ለአንድ ሰባት ወር እንደተቀመጥኩ አንድ ሽማግሌ ሰው እንዲህ ካለ ዋሻ ውስጥ የክርስቲያኖች መጽሐፍ አለ ብለውኝ አብረን ሄድን፤ ብዙ በብራና የተጻፉና የተቀዳደዱ መጽሐፎች አገኘን፤ እንደገና ከሌላ ዋሻ ሄደን ስንቆፍር ብዙ ፅላቶችንና ቁርጥራጭ ካባዎችን፣ ቁመቱ ክንድ አንድ መቶ ስልሳ አራት ብራና የአክሱማይ ሲራክን መጽሐፍ፣ የሱባን ቋንቋና የሱባን ታሪክ የያዘ መጽሐፈ ሱባኤ፣ እንደዚሁም በጣም የረዳኝ ሁለት መቶ ብራና አራት መቶ ገጽ ያለው የኢትዮጵያ ነገሥታት ታሪክ ዘግዱር ዘእንዳ ቤት በተፈለፈለ የድንጋይ ጉድጓድ ከተልባና ከአመድ ጋር ተቀብሮ ተገኘ፡፡
መጽሐፈ ሱባኤ ከአዳም እስከ ቀዳማዊ ምኒልክ መፀሐፈ አክማይ
ሲራክ ከቀዳማዊ ምኒልክ እስከ ዮዲት መጽሐፈ ታሪክ ነገሥት ዘኢትዮጵያ በዘግዱር ዘአንደበት የተጻፈ ከዮዲት እስከ በካፋ ልጅ ዳግማዊ ኢያሱ ከዳግማዊ ኢያሱ ወዲህ እስከ ኃይለ ሥላሴ ማህፀወ ነገሥት ከመሪጌታ ጉባኤ ጎጃም ሊበን ውስጥ ከተገኘ መጽሐፍ በብዙ ችግርና ድካ ለማሳተም ወደ ኢትዮጵያ በ1966 ዓ.ም. ይዤው ገባሁ፡፡››
(ከመጽሐፉ ጀርባ የተቀነጨበ)
‹‹… በጊዜው የነገሥታትን ታሪክ ማሳትና ማወደስ አደገኛ ነበር፡፡ ሁኔታውም በጣም አሰጋኝ፤ እናም ብዙ ሺ ማይልስ ከኔ ጋር ለብዙ ዓመታት ተንከራተተ፡፡ አሁን ጊዜውና አጋጣሚው ፈቅዶ አቋርጦ ከሄደበት ከምድረ አሜሪካ በሀገሩ በኢትዮጵያ በወንድሞቼ ብርታት ለመታተም በቃ፡፡ በዚህ አጋጣሚ አፈር የተጫናቸው መጻሕፍትና ንዋየ ቅዱሳት ቀስ በቀስ እየወጡ እውነተኛ ታሪካችን እየታወቀ እንደሚሄድ የዘወትር ጸሎቴ ነው፡፡››


ምዕራፍ ሦስት፡- ነገደ ኢትዮጵያ
‹‹ኢያስጴድ-ኢ፡ የኢትዮጵያ ዘመነ መንግሥት
ስሙ፣ አልፋ አየን አማን ኤል ኢያስጴድ፤
ፊደሉ፡ /እ/፣ /አ/፣ /ኣ/፣ /ኤ/፣ /ኢ/
/ኢትኤል ማለት የአምላክ ሥጦታ ማለት ነው፡፡/
የክህነቱ ስም ኢትኤል የተባለው ኢትዮጵ የአበ መለክስ ናምሩድ የልጅ ልጅ ነው፡፡ ናምሩድ አዳማን ወለደ፤ አዳማ ራፌልብን ወለደ፤ ራፌልብ ኬናን ወለደ፤ ኬና ወይም ቄና ጌራራን ወለደ፤ ጌራራ ወይም ጌራ ሃሙራቢ የክህነት ስሙ መልከጼዴቅ የተባለው ታላቁ የሰላም ንጉሥና የአምላክ አገልጋይ በደብረሣሌም ኢትን ወለደ፤ ኢትም እንዳባቱ አምላኩን ወዳድና ለፈጣሪው ታዛዥ ተገዥ ስለነበረ ኢትኤል ተባለ፤ ኢትኤል ማለት የአምላክ ሥጦታ ማለት ነው፡፡
ኢትኤልም በአምላኩ መንፈስ እየተመራ ግዮን ወንዝ ወደሚፈስበት ምድር ሄዶ ተቀመጠ፤ ያንም ምድር ኢያስጵድያ የሚባለውን ድንጋይና ከጥራቱ የተነሣ የሚያንፀባርቀው ኢያስጵድ ክርስቶ ድንጋይ ክብር ዮጵ ድንጋይ የሚገኝበት ነው፡፡ ስለዚህ ዮጵ በሚባለው ወርቅና በእንቁ ድንጋይ ሃብታም ስለነበረ ኢትኤል መባሉ ቀርቶ ኢትዮጵ ተባለ፤ ሚስቱም ሲና መባሉዋ ቀርቶ እንቅዮጳግዮን ተብላለች በነገደ ዮቅጣን አግአዝያን የሚባሉት አቡሳውያን እንቆ እንቁጳግዮን የሚባለው ስም እንቆዮጳዝዮን ብለውታል፤ ይሄውም የአባይ ወርቅ ማለት ቀርቶ የፅዮን ወርቅ እንዲባል ብለው ነው፡፡
ኢትኤልም ግዮን ወንዙን ለወንዝ አጠራቅሞና ሰብስቦ እስከሚገናኝበት ያለውን ምድር ሁሉ በስሙ ኢትዮጵያ እንዲባል አድርጓል በግዮን ዳርቻ ሄዶ የልጅ ልጆቹ በሚነግሡበት ጊዜ በዚህ ድንጋይ ላይ ተቀምጠው ቅባአ መንግሥታቸውን እንዲቀቡና እንዲነግሡ ሲል ኤለንኤል ብሎ በክብር ለማሳሰቢያ ትልቅ የድንጋይ ዙፋን አስቀምጧል፡፡ ይህም ምድር ከሳሌም እስከ ግዮን ድረስ የኢትዮጵ ልጅ አዜብ ይገዛው ስለነበረ አዜብ ይባላል፡፡
አዜብ መልከዘቦ ንጉሥ በግራ ክፍል የሚገኘውን የግዮን ገባሪ ሰማያዊ ግዮን ወንዝ እስከሚፈልቅበት ምድር ድረስ ግዛቱን አስፋፍቶ ስለነበረ ያ ምድር እስከ አሁን አዜብ ወይም አዘቦ ይባላል፡፡ አዜብያ በሚለው ሃገር ውስጥ አብርሃም ሳይባል አብራም ብዙ ቀናት በእንግድነት ተቀምጦበት ነበር አብራም በዚሁ ወርቅና በብር ከብሮበት ነበር፤ ይህም ታሪክ በሴም ነገዶች ተጽፎ ይገኛል፡፡ አዜብ 132 ዓመት ገዝቶ የኢትዮጵያ ታላቅ ልጅ አቲባ ወርካዘቦ ንጉሥ በቀኝ በኩል ያለውን የግዮን ገባሪ ወንዞች የሚፈልቁበትን ሃገሮች እንዲገዛ አንግሦ ሰደደው፤ አቲባም በአባቱ በኢትዮጵ ሥር ሆኖ እስከ ታላቁ ባህር በሚገኙት ጎሣዎች ላይ በሱባ አቆጣጠር ሰባት ሱባኤ ገዝቷል፡፡
ካህኑ ኢትኤልም በኢትዮጵያ ምድር ሆኖ ምድሪቱን ከባረካትና ለልጆቹም የመገናኛ ዘዴ ጽፎ ከአስተማራቸውና ሥርዓተ መንግሥት ከአሳያቸው በኋላ ንጉሥ ነገሥት በተባለ በአሥራ አራት ሱባኤ (98 ዓመት ማለት ነው)በተወለደ በአንድ መቶ አምሣ አንድደ ዓመት አንቀላፋ፤መልከጼዴቅ ከአስፈለፈለውና ከአሠራው ዋሻ ውስጥ ወስደው አስቀመጡት፤ በኢትዮጵ መጨረሻ የግዛት ዘመን እረሃብ ነበረና እብራውያን ወደ ምስር የተሰደዱበት ዘመን ነው፡፡
ኢትዮጵያ የተባለው ኢትኤል በፋቱራ የተድኦልን ልጅ እንቁጳን አግብቶ አሥር ወንዶች ሦስት ሴቶች ወለደ፡፡ የወንዶቹ ስማቸው አቲባ፣ ቦኦር፣ ቢኦራ፣ ተምና፣ ኤቴር፣ አሻን፣ አክለብ፣ መሪሣ፣ ቴስቢ፣ ቶላ፣ አቤሜሌክ የተባለው አዜብ ናቸው፡፡ ሴቶች ደግሞ ሎዛ፣ ሚልካና ሱባ ናቸው፡፡ የአቲባና የመጨረሻው ልጅ የአዜብ ዘሮች ነገሥታት ናቸው፡፡ የቢኦር ዘሮች መናፍስት በመጥራት፣ የተምና፣ የኤቴር፣ የአሻን ዘሮች የተለያዩ ቅርጾች በመሥራት የሰው ልጆች የሚያገናኙበትን፣ የሃሣባቸውን የሚገልጹበት ምልክት ወይም ጠልሰም ታሪክ የሚያቆዩበትን ጽሕፈት የሚያቆዩ ፈላስፎች ናቸው፡፡ ይሔውም ለመጀመሪያ ጊዜ በአምላክ ስም ፊደል የቀረጸ፣ ለእያንዳንዱ ቃል ትርጓሜ አቅርቦ ያስተማራቸው አባታቸው ኢትኤል ነው፤ ከዚያ በፊት የትውልድ ታሪክ በቃል ሲነገር በልብ ሲጻፍ ቆየ እንጂ ሌላ ዘዴ አልነበራቸውም፤ የአክዚብና የመሪሣ ዘሮች ናቸው፤ የቴስቤ ዘሮች የአምላክ አገልጋዮች፣ ትንቢት ተናጋሪ፣ መጭውን በማወቅ የታወቁ ናቸው፡፡ ከነዚህ ዘር የተወለደው ታላቁ ነቢይ ቴሰቢያዊ ኤልያስ ነበር፡፡ የቶላ ዘሮች አንጠረኞች፣ ግመሹ ነገዴዎች ነበሩ፡፡
ቢአር አራምን ወለደ፤ አራም ናጊን ወለደ፤ ናጌ ሃጌን ወለደ፤ ሃጌም ሁለተኛውን ቢኦርን ወለደ፤ ቢኦር በለአምን ወለደ፤ በለአም ከምሥር ዕብራዉያን ሲወጡ በእሥራኤል ላይ በመንፈስ እየተመራ ትንቢት ተናገረ፤ የተናገረው ቃልም እንዲህ አለ ‹አየዋለሁ አሁን ግን አይደለም፤ እመለከተዋለሁ በቅርብ ግን አይደለም፤ ከያዕቆብ ኮከብ ይወጣል፤ በእሥራኤል በትር ይነሣል፡፡ ከያዕቆብ የሚመጣ ገዥ ይሆናል› ሲል ስለ መሲሁና ስለ እረሱ ነገድ ደግሞ እንዲህ ሲል ትንቢት ተናግሯል ‹ማደሪያህ የፀና ነው፤ ጎጆህም በአምባ ላይ ተሠርቷል፤ ነገር ግን አሶር እስኪማርክህ ድረስ ቄናዊ (ኬናዊ) አንተ ለጥፋት ባርነት ትሆናለህ፤ አምላክህ ይህን ሲያደርግ አወደ፤ በሕይወት ማን ይኖራል፤ ከኪቴም ዳርቻ መርከቦች ይመጣሉ፤ ያስጨነቅህን አሦርንም ያስጨንቃሉ፤ ነገር ግን እርሱም ደግሞ ይጠፋል፡፡› ብሎ የተናገረውን ልጁ ደሸት ትንቢቱን ሲከታተል በቀትር ጊዜ ከምንጩ ዳር ተቀምጦ ፍልስፍናውን በአዝዋሪት ውሃ ሲያናና ሲፈለስፍ ለብልአም የታየው ኮከብ እንደገና ለደሸት ታየው የአዝዋሪቱን አረፋ ኮከብ እየተከታተለ ሲጽፍ ድንግል ሴት ያለ ዘር የተወለደ ልጅ ታቅፋ አያት፤ ወዲያውኑ ያየውንና ወደ ድንግሊቱ የመራውን ኮከብ ሥዕል በናስ ሰሌዳ ሥሎና ቀርጾና ድንግሊቱን፣ ልጅዋን እንደታቀፈች በወርቅ ሰሌዳ ሥዕሉን ቀርጾ ለልጆቹ አስቀመጠው፤ ሊሞት ሲል ‹ይህ ኮከብ የሚመስል በምሥራቅ በኩል ሲወጣ ዐይታችሁ፤ ጨረሩን ወደሚያመለክታቸሁ ምድር ተጉዛችሁ፣ ከምድራችሁ ከምታገኙት ከምታገኙት የምድር አበል ወርቅ፣ እጣን፣ ከርቤ፣ ልብስ ይዛችሁ ይህን አምላካችን ለአባታችን ለአዳም ለሔዋን እዲሰጣት የሰጠውን፣ አብርሃም ለአባታችን ለመልከጼዴቅ አሥራት ብሎ የሰጠውን እንአርያ በክብር ይዛችሁ፣ የኮከብ ብርሃን ለስግደት ሰግዳችሁ ስጡት፤ ሉልና ዮጴ የወርቅ ሃመልመላል ለእናቱ ስጡለት፤ ይህ እስከሚሆን ድረስ እንቆ አርያውን ተመልከቱት፤ እርሃብ ዘመን ሊሆን ሲል መልኩ ይጠቁራል፤ የጥጋብ ዘመን ሊሆን ሲል መልኩ ያበራል፤ ቅባቱ ይጭረቀረቃል ሲል እናተም ማርና ወተት ወደሚስባት ምድር ሔዳችሁ ትኖራላችሁ› ብሎ ለልጆቹ በተለመደ በአሥራ አንድ ሱባኤ ሞቷል፡፡ ይህም ዘመን በእሥራኤል ንጉሥ አልነበረም፡፡ በእሥራኤል ላይ የነገሠው ንጉሥ ዳዊትም በመንፈስ የታየውን ትንቢት እንዲህ ሲል ተናጋገረ ‹በፊቱ ኢትዮጵያውያን ይሰግዳሉ ጠላቶቹም አፈር ይለብሳሉ፤ የተርሲስና የደሴቶች ነገሥታት ሥጦታን ያመጣሉ፤ የአረብና የሳባ ነገሥታ እጅ መንሻን ያቀርባሉ፡፡ነገሥታት ሁሉ ይሰግዱለታል፤ አህዛብ ሁሉ ይገዙለታል፡፡› ሲል ከደሸት በኋላ ተናግል፤ ይህም ትንቢት ለመሲህ እንጅ ለሰለሞን አይደለም፡፡ ነገር ግን ከወርቅ በፊት ሰም ስለሚቀርብ ሰም የሰለሞን ወርቅ የመሲህ ትንቢቱ ተፈጽሟል፡፡
በልአም ሙት የምታስነሣ የነበረች የሸምሸልን አባት ቀራሚድን ወለደ፤ ዘጠኝ ወንዶችና ሴት ሸምሽልን ወለደ፤ ሸምሽል ፈላስፋው ደሸትን ወለደች፤ አባቱ አይታወቅም ይባላል (እዚህ ታሪክ አልፋለሁ)፤ የደሸት ልጆች ማጂ፣ ጅማ፣ መንዳና መደባይ ናቸው፡፡ የማጂ ዘሮች በኮከብ የሚያመልኩ፣ መንፈሰ ኃይል የተሰጣቸው መጭውን የሚናገሩ፣ በመንፈስ ስለመነጋገር የሚያምኑ ናቸው፤ ማጂ ማራን፣ ዣማን፣ ጂየማን ይወልዳል፤ ጂማ አረርቲን፣ ገነቲን፣ ሞረን ይወለዳል፤ እነዚህ ሁሉ የግዮን ምንጭ በሚፈልቅበትና በሚከበው ምድር ሄደው ሠፈሩ፤ በአባታቸው ስም ምድሩን ደሸት አሉት፤ ነገሥታት ደግሞ በንጉሥ ጎዣም በዳሞው ልጅ ስም ጎዣም ተብሏል፤ ይህም ስም የተቀየረ በዐፄ ዘመነ መንግሥት በአራት ሽህ አምስት መቶ ዓመት ከተቆጠረ (500 ዓመት ከክ.ል.በፊት) ነው፤ ማራ ከወገኖቹ ተልይቶ ቤተሰቦቹን ይዞ ወደ ፀሐይ መውጫ በተራሚው ሀገር ውስጥ ሄዶ ተቀመጠ፤ ገነት ኦዶምን ይወልዳል፤ ኤዶም ወደ ፀሐይ መውጫ ወደሚገኘው ባሕር ሄዶ መኖሪያውን አደርገ፡፡
ቀለመ ዮጵ የተባለው ዘግዱር የዣማን ነገዶች ግማሹን ታሪክ ፀሐፊ አድሮጎ ቤተአንዳ የዛሬ አንዳ ቤት ግማሹን የመደባይ ነገዶች ቦረኖች ወደሞኖሩበት ቤተማራ የዛሬው መርሃቤቴ ላካቸው፤ ያንም ሃገር በአባታቸው ስም ወንዙን ዣማ አሉት፤ በዚያንም ሃገር የማሩ ነገዶች ይኖሩበታል፤ እነዚህ ማሩ የተባሉ ሁለተኛው ዘግዱር አሚንሆ የተባለውን የእብነልሃኪም የልጅ ልጅ በግብጾች ጋር በአደረገው ጦርነት ለእርዳታ ሄደው በዚያው ቀርተዋል፡፡ ያም የሠፈሩበት ሃገር አማርና ይባላል፡፡ ከሁለት ሺህ ዓመታ በላይ ከኖሩ በኋላ በዐፄ ላሊበላ ዘመነ መንግሥት ከግብፅ ወደ ኢትዮጵያ መጥተው በቤተሃማራ ከሚኖሩት ጎሣዎቻቸው ጋር ተቀላቅለው ኖሩ እነዚህም የዛሬዎች አማራዎች ናቸው፤ ከነገደ አማራ ኢትዮጵ አቲባን ወለደ፤ አቲባ ሁለትኛው አዜብን ከሣዱንያ ልጅ ቂቂ ከምትባል ንግሥት ወለደ፤ አዜብ ሰቢን ወለደ፤ ሰቢ በግዮን ዳርቻ ስመ መንግሥቱ ሞረሽ መለከ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ ተብሎ በሃያ አንድ ነገሥታ በአርባ አምሰት ሀገሮች ላይ ነገሠ፤ ግዛቱም በስሙ ሞሪያ ከተባለው ተራራና እስከ ከሱኪ ባሕር ድረስ ነው፡፡ ሞረሽ መለከ ሠራዊቱን ሃገር እንዲያቀኑ፣ ግዛት እንዲያስፋፋ ወደ መካከለኛው ግዮንና ወደ ታላቁ ባሕር ላካቸው፤ እነሱም ምድሩን እርስት አድርገው በዚያው ቀርተዋል፤ በስሙ ምድሩን ሙርታንያ፣ ሕዝቡም ሞረቴ ተብለዋ፤ ግዛቱም ሰባ ሰባት ዓመት ነው፤ በፈንታው ልጁ ልብና ነገሠ፡፡ ሞረሽ መለክ የተባለው የአዜብ ልጅ ሳቢ በሙርታንያ ልብናን ወለደ፤ ልብና በግዮን ዳርቻ ስመ መንግሥቱ ሊባኖ ተብሎ በኢትዮጵያ ምድር ሁሉ አርባ አራት ዓመት ነገሠ፤ ልብና ከፍልስጢሞችና ከአማሌቅ ጋር ሲዋጋ በጌራራ ሞተ፤ ለልብና አንድ ልጅ ስለነበረው በፈንታው ሱካውያንን፣ አዜባውያን አነገሡለት፤ በነገሠ በሦስት ዓመት የአባቶችን ሕግና ሥርዓት ለመፈጸም በግዮን ዳርቻ እንደገና ነገሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ ተብሎ ዳግመኛ ነገሠ፤ ግዛቱም ሦስት ሱባኤ ተኩል (ሃያ አራት ዓመት) ነው፡፡ አቤሜሌክ የተባለው መሌክ ጋዝያን በጌራራ ወለደ፤ ጋዜያም በአባቱ ፈንታ አበሰኒ ተብሎ በሲና አዜባውያንና ሱካውያን አነገሡት፤ በጋዝያ ዘመነ መንግሥት ብዙ ሕንፃ ተመሠረተ፤ ያነንም ምድር በስሙ ጋዛ ተባለ፤ ግዛቱም ሰባት ሱባኤ ነው፡፡ ይህም አርባ ስምንት ነው፡፡ አቢሲኒ የተባለው ጋዝያ አድያምን ወለደ፤ አድያም በግዮን ዳርቻ ስመ መንግሥቱ ላክንዱን ተብሎ በኢትዮጵያ ምድር ነገሠ የግዛቱም ዘመን ሰማንያ ሦስት ዓመት ነው፤ ላክንዱን የተባለው አድያም ታላቁ ንጉሠ ነገሥትን ታንዛን ወለደ፡፡
እንደዚህ ሆነ የአድያም ልጅ ታንዛን አሥራ ሁለት ወንዶች፣ አሥራ ሁለት ሴቶች ከአራት ሚስት ወለደ፤ የወንዶች ሰማቸው ስኒ፣ ጉሚዚ፣ ጉድሪ፣ ኩንፍ፣ ከፊን፣ ጎም፣ ከሬች፣ ጉፍ፣ ሓማ፣ ዝሪ፣ ሣምሪ፣ ዮቶሮ፤ የሴቶቹ ስም ካሳኪ፣ ቲካ፣ ዩኒና፣ ብሌኒ፣ ቢሸሎ፣ ችልጋ፣ ልሄም፣ ሳለታ፣ ኤፍራታ፣ ወልቃ፣ ቆቂና፣ ነገዶች ናቸው፤ እነዚህ ሁሉ አባታቸው ኢትዮጵ ንኤል የሚባል ታላቅ ድንጋይ ለማሳሰቢያ በአስቀመጠበት በግዮን ዳርቻ ሳለ ተወለዱለት ታንዛን ስመ መንግሥቱን ንርአስ አሰኝቶ በግዮን ዳርቻ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ ተብሎ በነገሠ ጊዜ በሥሩ አራት ንጉሦች ሲያነግሡ ታላቁ ልጁን ሲኒን በኩርነት የመጨረሻውን ልጁን ክህነትን አምላኩን እንዲያገለግል ሁለቱን የአባቶችን አፅም እንዲጠብቁና በቦታው እንዲተኩ ወደ እርስታቸው ወደ ምድያም ላካቸው፤ ሌሎቹን ሴቶችና ወንዶችን ይዞ ከብዙ ሠራዊት ጋር ወደ ተራራማው ሃገር ሄዶ ቤተ መንግሥቱን ቆረቆረ፤ ስምዋንም ዋይዝ አላት፤ የታንዛንያ ልጆች ያገኙት ምደር ዝፍ፣ የምንጭ ውሃ፣ ታላላቅ ወንዞች የሚገቡበት ለምለም መሬት ሆኖ የዛፍ ፍሬ ለመልቀም አመቺ ስለነበረ በመካከላቸው ጠብና ግጭት እንዳይኖር ለሃያ ሁለት የታንዛኒያ ልጆች ተካፈሉት፤ ከነሱ ቀጥለው የማጂ ልጅ ሄደ፤ መደባይ የማራን ልጆች ሃገር አልምተው ነበርና ጦርነት ቢያነሱ ሊተባበሩ በታላቅ ተራራ ሥር በደጋው መሬት ቃል ኪዳን አደረጉ፤ በየደረጃቸው የታላቅነትና የታናሽነት ምልክት የሚገልጽ የማንኛው ልጅ መሆናቸውን የሚያስረዳ ክትባት አደረጉ፤ ፊታቸውን ተቆረጡ፤ የመጀመሪያው ልጅ ሲኒ ወደ ምድያም ስለሄደ የቁርጡ ክትባት ምልክት በሁለት ይጀምራል፤ ይሄውም የመጀመሪያውና የሁለተኛው ልጆች መሆናቸውን የሚገልጹትበት ቁጥር ነው፡፡ II-III እያለ እስከ ሰባት ሲደርስ እንደገና በግንባራቸው ላይ ክብ ዓይነት ቆረጣ ያደርጋሉ፡፡
ከነዚህም ሖማ የተባለው የገላው ቆዳ በጣም የጠቆረ ቁመቱ ረጂም አስፈሪና አስደንጋጭ ነበረ፤ ሖማ ማለት በሱባ ‹የእውነት ዛፍ ነህ› ማለት ነው፡፡ የሖማ ልጆች ጎጂ፣ ጂን ሻቃ፣ ጅንጀር፣ማሴሻ ናቸው፡፡ ሻቃ ጠንካራና እንደአባቱ አስፈሪ ጥቁር ነው ትርጓሜውም የአምላክ ትንፋሽ ማለት ነው፤ ሻቃም በአባቱ ሥር ሆኖ በግዮን ዳርቻ እስከ ደሸት ድረስ አራት ሱባኤ ተኩል ገዝተዋል፡፡ የሆማ ልጅ ጀንጀር ፈጣኑ ርዋጭ ናይጀርን ወለደ፤ ናይጀርም አያቱ ታንዛን ባርኮና አንግሦ ግዛ ብሎ እስከ ታላቁ ባሕር ድረስ ፈቀደለት፤ ንጉሥ ናይጀርም የሄደበትን ሃገር ወንዝ በስሙ ናይጀር እንዲባል አድርጓል፡፡ አልጀር ብሂል ርዋጭ የሖማ ልጅ ማሊ መሣይ ካህን ስለነበረ አያቱም እንደ ቶርአብም ክህነትን ስለባረከለትና በፈቀደውና በወደደው መሬት እንዲቀመጥ ስለፈቀደለት የሄደበትን ሃገር በአያቱ ስም ታንዛን አለው፤ ልጆቹ የቡራኬን ሥራ አጥብቀው የሚወዱና የሚፈቅዱ ናቸው፤ መሣይ በቡራኬ ቀን ንፅሕ ተላጭተው በጆሯቸው ጌጣጌጥ እንጥልጥል አድርገው ይቀርባሉ፤ ሕግና ሥርዓት ሆኖ እስከዛሬ ድረስ አለ፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን ሖማ በግዮን ዳርቻ መኖሪያውን አደረገና ከዛፍ ሥር ተቀምጦ ሳለ መልኩዋ የሚያምር የሚያንፀባርቅ ልብስ ለብሳ አንዲት ሴት ልጅ ከባሕሩ ውስጥ ወጥታ ከአለበት ዛፍ መጥታ እንደጥላ ሆና ስትገባ አያትና ቢፈልግ አጣት፡፡
ከዚያ ወደቤቱ ሳይሔድ ከወገኖቹ ተለይቶ በዛፍ ሥር ለብዙ ቀን ከኖረ በኋላ ተገለፀችለትና ለምንድነው ይሄን ያክል ቀን የተቀመጥከ አለችው፤ አፍቅሬሽ አላት፤ ከአፈቀርከ(ኝ) አግባኝ ብትለው አፍቅሯት ነበርና እሺ አላት፤ ስምህ ማነው ብትለው ሖማ አላት፤ ይህም ዛፍ ሖማ ነው አለቸው፤ ያንቺስ ሺባ እባላለሁ አለችው፤ ተጋብተው ብዙ ዓመታት ከሆናቸው በኋላ የወገኖቹ ሴቶች ልጆች ጂና፣ ጃንካ የሚባሉ አደን ሄደው ሳለ አገኙትና ለምን እንደጠፋና ወደ ቤቱ የማይሔድበትን አጥብቀው ጠየቁት፤ እሱም ሁሉን ነገር ገልጾ ነገራቸው፤ እነሱም አብረው እንዲኖሩ ቢጠይቁት ሺባ ባለቤቱን አስፈቅዶ አብረው ከወገኖቻቸው ተለይተው እንዲኖሩ አደረገ፤ ከዚያም ሁለቱን በሥጋ አጋባቸውና ልጅ ወለዱለት የሖማ የልጅ ልጆች እየበዙ እንደሄዱ ሲያውቁ በዘራችን ያለአምልኮት አንኖርምና ስለዚህ ከወገኖቻችን ሄደን የምናምልክበትን ነገር እናምጣ አሉዋት ለሺባ፤ እሷም እኔን ብታመልኩ መአት ቢመጣ እስወራችኋለሁ፤ የምትፈልጉትን ሁሉ እሰጣችኋላሁ፤ ስለአምልቱ ሥርዓት አባታችሁ ያሳያችኋል አለቻቸው፡፡
ሆም ሆማም እሚያመልኩበትን ጌጥ በጥቁር እንቁ አሠርቶ ሸባሻንቃ ለወንዶች ልጆች፣ ሻንቀል ለሴቶች ልጆች ማለኪያ አደረገላቸው፤ ወደ ሻበሻንቅና ወደ ሻንቀል ለአምልኮት የሚገቡ ሁሉ ክሰል ፈጭተው፣ አልመው ከቡልቃ ፍሬ ጋር ለውሰው ተቀብተው መግባት አለባቸው፤ ሴቶች ደግሞ ጥቁርና ቀይ አፈር ከቡልቃው ፍሬ ዘይት ጋር ለውሰው ተቀብተው ይገባሉ፤ ይህም የአምልኮ ባሕልና ልማድ እስከዛሬ ድረስ አለ፤ ከቡዳና ከሂንዱ ሃይማኖት ጋር ይስማማል፤ ከነዚህ እንደመነጨ የሚያስረዳው የህንዶች እምነት ከዚህ የተያያዘና ሺባ በጣም በህንዱ የታወቀች ናት፤ ሺባ የምትባለው ነጭ ነገር ስለምጠላ ዛፍ ደርቆ ቅርፊቱን በሚጥልበት ሰዓት በቶሎ እንዲጠቁር ያቃጥሉታል፤ ከነሱ መሃል ነጭ ቆዳ ሰው ቢወለድ ገለው ይቀብሩታል ወይም ያቃጥሉታል፤ ይችውም የመንፈስ ዛር ታምርን በመሥራት ከአደጋ ነገር በመሰወር የታወቀች ስለነበረች ሃንዲ የሚባሉ ጎሣዎች ወርቅና ልጃቸውን ስእለት በየጊዜው ይሰጡዋት ነበር፤ ሻቃ የሚባለው በመንፈስ እናቱ ሸበሻንቃ በተባለው ማምለኪያ የታመነ ስለነበረ ወርቅና በከብት የከበረ ሆኖ መቀመጫውን በግዮን ወንዝ አደረገ ልጆቹም በአባታቸው ስም ሻንቅላ ተባሉ፤ ወንድሞቹም ጀንና ሉቅ በዋሻና በድንጋይ ሥር ቤታቸውን አደረጉ፤ ባህላቸውም ከታላቁ ወንድማቸው ጋር ተመሳሳይ ሆነ፤ በጋብቻቸው ጊዜ ከጂን፣ ከሉቅ ልጆች ጋር ሴት በሴት ተቀያይረው ይጋባሉ፤ ሴት እህት ከሌለው አንዱ ከነሱ ዜጋ ውጭ የሆነውን ሰው ገሎ ሰለባ በማድረግ ሰለባውን አሳይቶ ሴት ማግባት ይችላል፡፡ ጀግንነቱ፣ ክብሩ፣ ሹመቱ ሁሉ በነሱ ዘንድ ሰለባ ብቻ ነው፤ ሌላ በኩርነት ያለው አለቃ መሪ ሊሆን ይችላ፡፡
እነዚህ ጎሣዎች የዛፍ ፍሬ ለቅመው ሥር ቆፍረው የአገኙትን አውሬና በራሪ ወፍ አሞራ ገድለው ከመብላት በስተቀር ከብት አርብተው አታክልት ተክውለው አያውቁም ነበር ነገር ግን የሚሠሩት ነገር ሁሉ በህብረት ነው፡፡
ኖርኡስ ታንዛን ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ በተባለ በሰማኒያ አምስት ዓመቱ ዕብራውያን ከግብፅ አርነት ነፃ ወጡ ወደ ከነዓን ርስታቸው በተመለሱ በሦስተኛው ዓመት በተወለደ በመቶ ሠላሳ አንድ ዓመት አንቀላፋ፤ በፈንታውም በሲና በረሃ የሚኖረው ራጉኤል የተባለው ታናሹ ልጅ ዮቶር በግዮን ዳርቻ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ ተብሎ ነገሠ፤ በምድያምና በሲና ምድር የኤልሻዳይ ካህን የክህነቱ ራጉኤል የተባለ የታንዛን ልጅ ዮቶርአብ የሚባል ነበር፡፡
ለዮቶርአብ አሥር ወንዶች፣ ሰባት ሴቶች ነበሩት፤ ወንዶች ኤልሳ፣ ዛሆ፣ ኡሪኤል፣ ንስኤል፣ አልባኤል፣ አልባ፣ ኤልሃ፣ ዙርባኤል፣ ተውሳ፣ አባብሂር፤ ሴቶች ሲፖራ፣ ልሂ፣ ዘሃራ፣ ተምና፣ ለውይዛ፣ እሰድ፣ ዘኒባ ናቸው፡፡ እነዚህ ሁሉ በምድያም ምድር ተወለዱለት፡፡
የኤል አገልጋይ፣ የምድያም ካህን ራጉኤል በምድያም ምድር የአባቶችን ታሪክና ስም የያዙና፣ የፈጣሪን ቸርነትና ረዳትነት የሚገልፁ መጻሕፍትን በበግ፣ በፍየል፣ በፈረስ ቆዳ ጻፈ፤ ጽሕፈት በኢትኤል ተጀምሮ በልጆቹ በሥነ ሥርዓት ቢያዝም ከአጥንትና ከእንጨት ከተሠራ ሰሌዳ ላይ ከመጻፍ በስተቀር በብራና ተፅፎ አያውቅም ነበር፡፡ ራጉኤል በብርና በወርቅ በከብትም ከመክበሩ ሌላ በአስተዋይነቱና በጥበቡ ብዛት በሞአብና በአሞን ልጆች በአማሌቅም ሎጆች በፌርዛውያውን፣ በአሞራውያን፣ በከነአናውያ፣ በአቡሳውያን ታውቆ ነበር፡፡ ጥበቡን ለማየት፣ ዕውቀቱን ለመማር ወደ እርሱ ይሄዱ ነበር፡፡ ከነዚህም ከግብፅ ተነሥቶ ወደ ራጉኤል ከሄዱት አንዱ ሙሴ ነበር፡፡ ሙሴም በራጉኤል ቤት ሳለ የአምላክ አገልጋይ ካህንና ትሁት ሰው ለመሆን ይተጋ ነበር፡፡ የምድያም ካህን ራጉኤልም የአምላክ ሰው መሆኑን አስተውሎ ታላቋን ሴት ልጁን ሲፖራን ለሙሴ አጋብቶ በቤተ መቅደሱ ላይ ሾመው፤ ሙሴም ብዙ ቀናት አብሮት ተቀመጠ፡፡
እንደዚህም ሆነ፣ ግብፃውያን በዕብራውያን ላይ የሚያደርጉትን ግፍ የእሥራኤል አምላክ ተመለከተ፤ የዕብራውያን ሃዘንና ጸሎት ወደ አምላክ ደረሰ፤ ስለዚህ አምላክ በግብፃውያን አርነት እጅ ሕዝቡን እሥራኤልን ያወጣ ዘንድ ለሙሴ በአምላክ ተራረራ በኮሬብ በነበልባል ውስጥ የአምላክን መላክ ዐየ፤ ሙሴም ወደዐየበት ዛፍ ተጠጋ፤ በነበልባሉም ውስጥ እንደዚህ የሚቃል ሰማ ‹ሙሴ ሙሴ ሆይ ወደዚህ አትቅረብ፤ የቆምክበት ሥፍራ የተቀደሰ መሬት ነው፤ በቅድሚያ የአቡውያን ትምህርት የሆነ ጫማህን ከእግረልቦናህ ፈጽመህ አውጣ፤ ደግሞም እኔ የአባቶችህ አብረሃም፣ የይስሐቅ፣ የያዕቆብ አምላክ ነኝ› አለው፡፡
‹ሕዝቤን ዕብራውያንን ከግብፅ ምድር ታወጣ ዘንድ ወደ ፈርኦን እልክሃለሁ፤ እኔም ከአንተ ጋር እሆናለሁ፤ እኔም የላክሁህ ምልክቱ ይህ ነው፤ ሕዝቤን ከግብፅ ምድር ባወጣህ ጊዜ በዚህ ተራራ ላይ ለአምላካችሁ ትገዛላችሁ› አለው፡፡ ሙሴም የአባቶችን አምላክ ቃል ሰምቶ ወደ ግብፅ ወረደ፤ ከዚያም በብዙ ታምር ዕብራውያን ከግብፅ አርነት አውጥቶ በአምላክ ረዳትነት ተመልሶ መጣ፤ በዚያም አማቱ ራጉኤል በአምላክ ተራራ በኮሬብ ወደ ሠፈረ ሙሴ መጣ፤ ሙሴንም እኔ አማትህ ዮቶር አብ፣ ሚሰትህ ሲፓራ ፣ልጆችህ ጌርሳም አልኣዛር መጥንልሃል አለው፤ ሙሴም አማቱን ሊገናኝ ከድንኳን ወጣ፤ ሰገደም ሳመውም፤ እረስ በራሳቸው ደኅንነታቸውን ተጠያየቁ፤ ወደ ድንኳን ገቡ፤ ሙሴም አምላካቸው በግብፅ ባለሥልጣኖችና በፈርኦን ላይ ስለ ዕብራውያ ያደረገውን ሁሉ በመንገድም ያገኛቸውንም ድካም ሁሉ ኤልሻዳይ አምላክ እንዳዳናቸው ለአማቱ ነገረው፡፡
ካህኑ ራጉኤልም ለዕብራውያን ስላደረገው ቸርነት ሁሉ ደስ አለው፡፡ ራጉኤል በሙሴና በዕብራውያን ስላደረገው ቸርነት ሁሉ ከግብፅውያን አርነት ስለዳናቸው ደስ አለው፡፡ ራጉኤልም በሙሴና በዕብራውያ ሽማግሌዎች መካከል ቁሞ፤ እጁን ዘርግቶ እንዲህ አለ ‹ከግፅውያና ከፈርኦን እጅ ሕዝቡን ያዳነ የእሥራኤል አምላክ ይባረክ፤ አልሻዳይ አምላክ ከአማልክት ሁሉ የበለጠ የእሥራኤል አምላክ እንደሆነ አሁን አወቅኩ› አለ፤ እንደዚህም ብሎ የእህል መስዋእት ስንዴና ወይን በአባታቸው በመልከጼዴቅ የታዘዘውን ሁሉ የሚቀጠለውንም የሚጤሰውንም ለአምላ ወሰደ፤ ሁለቱም በአንድ ላይ መሥዋዕትን አቀረቡ፤ ኤልሻዳይ አምላካቸው መስዋዕታቸውን ተቀበለ፤ የሚቃጠለውን ሁሉ ከሰማይ እሳት ወርዶ በላው፤ በአምላካቸው ፊት ከሙሴ ከአማት ጋር የዕብራውያን ሽማግሎዎች የመሥዋዕት እንጀራ ሊበሉ መጡ፡፡
እንደዚህም ሆነ በነጋው ሙሴ በሕዝብ ሊፈርድ ተቀመጠ፤ ሕዝቡም ከጥዋት እስከ ማታ ድረስ በሙሴ ፊት ቁመው ነበረ፤ ራጉኤልም በሕዝቡ ሙሴ ያደረገውን በየጊዜው ይህ በሕዝብ የምታደርገው ምንድነው? ሙሴም አማቱን ሕዝቡ አምላክን ለመጠየቅ ወደ እኔ ይመጣሉ፤ ነገርም ቢኖራቸው ወደ እኔ ይመጣሉ፤ በዚህና በዚያ ሰውም መካከል እፈርዳለሁ፤ የአምላክ ሕግና ሥርዓትንም አስታውቃቸዋለሁ አለው፡፡
ራጉኤልም አለው ‹አንተ የምታደርገው ይህ ነገር መልካም አይደለም፤ ይህ ነገር ይከብደሃል፤ ሕዝቡም ይከብደዋል፤ አንተ ብቻህን ልታደርገው አትችለም፤ አሁንም እመክርሃለሁ፤ ቃሌን ስማ፤ አምላክ አንተ ጋር ይሆናል፤ አንተ በአምላ ፊት ለሕዝቡ ሁን፤ ነገራውንም ወደ አምላ አድርስ ሥርዓቱንም፣ ሕጉንም አስተምራቸው፤ የአምላን ሕግና ሥርዓቱን በቃልህ ሰምተው የሚጽፉ ጸሐፊዎች አዘጋጅላቸው፤ በጆሯቸው ጠዋትና ማታ የሚነግሯቸውና የሚያስተምሯቸው ዐዋቂዎችን ምረጥላቸው፤ የሚያደርጉትንም ሁሉ ለአስተማሪዎች አስተምራቸው፤ ስለነጋራቸውም ደግሞ እንደዚህ አድርግ ከሕዝቡ ሁሉ ዐዋቂዎችን አምላክን የሚፈሩ፣ የታመኑ፣ የግፍን ሥራ የሚጠሉ ሰዎች አስመርጥ፤ ከእነሱም የበላይ አዛዥ፣ የሺህ፣ የመቶ፣ የዓምሣ፣ የአሥር አለቆች ሹምላቸው በሕዝቡ ላይ ሁልጊዜ ይፍረዱ፤ ለመፍረድ የማይችሉትን ወደ አንተ ያምጡት፤ ታናሹን ነገር ሁሉ እነሱ ይፍረዱ› አለው፤ ‹ይህ ነገር ለአንተ መልከም ነው፤ ይቀልሃል፤ ይህንም ፈጽመህ ብታደርግ አምላክ ቢያዝህ መቆም ትችላለህ፤ ይህ ሕዝብ ደግሞ በሰላም ወደ ሥፍራው ይደርሳል፤ የነመልከጼዴቅ፣ የነኢትኤልም ሕግና ሥርዓት እንደዚህ ነው› አለው፡፡
ሙሴም የአማቱን የራጉኤልን ቃል ሰማ፤ ያለውንም ሁሉ አደረገ፤ ሙሴም ዐዋቂዎችን ሁሉ መርጦ በሕዝቡ ላይ የበላይ አዛዥ፣ የሺህ አለቃ፣ የአምሣ፣ የአሥር አለቃዎች፣ጸሐፊዎችና አስተማሪዎች ሁሉ አዘጋጀና ሾመላቻ፤ በሕዝቡም ላይ ፈረዱ፤ የከበዳቸውን ነገር ግን ወደ ሙሴ አመጡ፤ ከዚያም ሁለቱ በሰላልም ተሰነባበቱ፡፡
ከዚያም የክህነቱ ስም ራጉኤል የተባለው ዮቶር አብ በተወለደ በስልሳ ሰባት ዓመቱ ዕብረውያን ከግብፅ በወጡ በሦስት ዓመት አባቱ ኖርኦስ ታንዛን ስለሞተ በግዮን ወንዝ ዳርቻ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ ተብሎ ነገሠ፤ በነገሠ በሃያ ሁለት ዓመቱ አንቀላፋ፤ ከእሱ ቀጥሎ በፋንታው ልጁ አባብሂር ዕብራውያን የረዳ መንገድ የመራቸው ስለነበር ከዕብራውያ ወገን የምትሆን የአሚን አዳብ ልጅ ሩት አሚን የምትባለውን አግብቶ ወደ ግዮን በሚያወርደው ምድር ተቀመጠ፤ በዚያም ኢትዮጵስን ወለደ፤ ስመ መንግሥ ሰንደቅ ዣን ተብሎ በግዮን ዳርቻ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ ተብሎ በነገሠ በሰባተኛው ዓመት ታላቁን ከተማ ሱባን ሠራ፤ በሱባም ታላላቅ ግንቦች ተገነቡ፤ የውሃ መከማቻ ጉድጓዶች ተዘጋጁ፤ በምድርም እንደሱባ ያለ ከተማ አይገኝም ነበር፡፡
ኢትዮጵስ የሱባውያ ንጉሥ ናኦድ በእሥራኤል ላይ መስፍን በነበረ ጊዜ በሳሌምና በአካባቢዋ የሚኖሩ መንደሮች ያለ ጦርነት በሰላም ኖሩ፤ በሱባ የሱባ ንጉሥ ኢትዮጵስ በዘመኑ ምድር ከማካፈልና ከተማ ከመቆርቆር የሀገር ስም ከማውጣት በስተቀር ጦርነት አድርጎ አያውቅም፤ ልጁን ሄቤርን በቃዴስ፣ በፀእናይ መካከል አንግሦት ስለነበር ዕብራውያንና የቃዴስ ንጉሥ ቃል ኪዳን ስለነበራቸው የሄቤር ሚስት ኢያኤል የምትባለው የኢያቤስን የጦር መሪ ሢሠራን ገደለችና የግድያውንም ምልክት እራሱን ለእሥራኤል ልጆች ሰጠች፤ በዚያም ዕብራውያን ስለተደረገላቸው እርዳታ አምላካቸውን አመሰገኑ፤ በሄቤርቤትና በእሥራኤል ልጆች ቤት ወዳጅነታቸው ፀና፡፡ ኢትዮጵስ ሰንደቅ ዣን በየ በርሃው መንደር እየቆረቆረ ሴት አግብቶ በቆረቆረው መንደር ሁሉ ማስቀመጥ ይወድ ነበር፡፡ ስለዚህ ንግሥት የተባሉት ሰባት ሰለነቡ አምሣ ልጆች ከነሱ ወለደ፡፡ እነዚህም አሥራ ሦስት የነገሡ ናቸው፡፡ እነዚህም የኤብያ ንጉሥ ኦማም በአዜብ በርሃ የምትገኝ መንደር የመጀመሪያቱ ሳባ፣ የሳባ ንግሥት ቲራ፣ የኦፊር (የዛሬው ውጋዴን) ንጉሥ ሸሚዳ፣ የኤውላጥ ንጉሥ ሃሺሞን፣ የመደባይ ንጉሥ እናርያ ኋላ በስሙ እናሪያ የተባለው የዛሬው ሊሙ፣ መደባይ መንዲ የሚባሉት የዛሬዎቹ ኦሮሞ አልብኖ ናቸው፤ የመንዲ ንጉሥ ኢያቢስ፣ የኪና ንጉሥ ጂማ፣ የልብስኖ ኑጉሥ ስልባኖን፣ የቃዲ ንጉሥ ሄቤር፡፡
በሰንደቅ ዣን ሰር ወይም ዙፋን ወራሹ ኤልካኖ፣ በሰብያ የሱባ ኑግሥ ሲሆኑ አሥሩ ወንዶች ናቸው፤ ሴቶች ደግሞ የአዲን ንግሥት በለሣ፣ የኤደን ንግሥት አሊና፣ ከሁሉም ልጆቹ በላይ ይወዳት የነበረችውን ኢትግዝያ ከግዮን መገናኛ እስከ ሱኪ ድረስ ባለው በሊብያ ምድር ሁሉ አነገሣት፤ ንግሥተ ነገሥታ ዘኢትዮጵያ የሚል የማረግ ዘውድ በራስዋ ላይ ደፋች ኢትግዝያም በአባትዋ ሥር ሆና አርባ አምስት ዓመት ከገዛች በኋላ በተራራማው ሃገር ዋሻ ውስጥ ሄዳ ተቀመጠች፤ ያንንም ሃገር ያማራ ዜጎች የሚኖሩበት ምድር ነው፡፡
ሰንደቅዣን የተባለው ኢትዮጵ ስም አርባ ስድስት ዓመት በክህነት እስከ ታላቁ ባሕር ድረስ አሥር ዓመት ገዝቶ በመልካም ገዜ አረፈ፤ በፈንታውም ልጁን ኤልካኖን ስም መንግሥቱን በአባቱ ስም ኢትዮጵስ ተብሎ በግዮን ወንዝ ዳርቻ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ ከኪቲም እስከ ታላቁ ባሕር ውስጥ በሚገኙት ደሴቶች ሁሉ ላይ ነገሠ፡፡››
Source: http://kassahunalemu.wordpress.com/

No comments:

| Copyright © 2013 Lomiy Blog