የጠላፊው ረዳት አብራሪ ጉዳይ አነጋጋሪ ሆኗል

-  መንግሥት ተላልፎ እንዲሰጠው ይፈልጋል:
ባለፈው እሑድ ሌሊት 6፡30 ሰዓት ከአዲስ አበባ ወደ ሮም መብረር የጀመረውን የበረራ ቁጥሩ ‹‹ET 702›› የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቦይንግ 767 አውሮፕላን የጠለፈው ረዳት አብራሪው ኃይለመድኅን አበራ ተገኝ ጉዳይ አነጋጋሪ ሆኗል፡፡
ጠለፋውን ፈጸመ የተባለው ረዳት አብራሪ ቤተሰቦች መሆናቸውን የሚናገሩ፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በኃይለመድኅን ላይ ያልተለመዱ ባህሪዎችን መመልከታቸውን ይናገራሉ፡፡
ለኢትዮጵያ አየር መንገድ ቅርብ የሆኑ ምንጮች ደግሞ ግለሰቡ በተለያዩ ጊዜያት የዲስፒሊን ችግሮች ቢኖሩበትም፣ ብቃት ያለው አብራሪ እንደነበረ ገልጸዋል፡፡
ጉዳዩን በተመለከተ ባለፈው ሰኞ ከቀትር በኋላ መግለጫ የሰጡት የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሚነስትር አቶ ሬድዋን ሁሴን፣ ግለሰቡ ጠለፋውን ለመፈጸም ምን እንዳነሳሳው እንቆቅልሽ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
‹‹አንድ ሰው በጠለፋ ወንጀል ከተሰማራ ቢያንስ 20 ዓመት ነው የሚፈረድበት፡፡ ከ20 ዓመት በኋላ ምን እንደሚያትርፍ ለጊዜው የታወቀ ነገር የለም፤›› ያሉት ሚኒስትሩ፣ ምን ዓይነት ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች እንደገፉት ለማወቅ ምርመራ መጀመሩን ገልጸዋል፡፡
ረዳት አብራሪ ኃይለመድኅን የ31 ዓመት ወጣት ሲሆን፣ በአየር መንገዱ ለአምስት ዓመታት ያገለገለ መሆኑን የጠቆሙት አቶ ሬድዋን፣ በግለሰቡ የግል ሕይወት ዙሪያ በምርመራ የተደረሰበት መረጃ በአሁኑ ወቅት እንደሌለ ጠቁመዋል፡፡

‹‹የረዳት አብራሪውን የግል ሕይወት በተመለከተ ዝርዝር መረጃ በአሁኑ ወቅት የለም፡፡ ለጤንነት የማያሰጋ ሁኔታ ነበር ወይ የሚል መረጃም የለም፤›› ብለዋል፡፡
በበረራ ኢንዱስትሪ ውስጥ የበረራ ደኅንነት ከፍተኛ ትኩረት የሚሰጠው እንደሆነ ይታወቃል፡፡ በመሆኑም አየር መንገዶች የበረራ ሠራተኞቻቸውን ጤንነት በየጊዜው እንደሚከታተሉ ለበረራ ኢንዱስትሪው ቅርበት ያላቸው ይናገራሉ፡፡ ሙሉና ጥልቅ የሆነ የጤና ምርምራ በየስድስት ወራት በበረራ ሠሪተኞች ላይ እንደሚደረግ፣ ድንገተኛ የጤነንት ምርመራ ደግሞ በማንኛውም የበረራ ሠራተኛ ላይ በድንገት ሊደረግ እንደሚችል ገልጸዋል፡፡
አውሮፕላኑን ጠለፈ በተባለው ረዳት አብራሪ ላይ የተደረገ የቅርብ ጊዜ የጤንነት ምርመራ ውጤት መረጃዎች ምን እንደሚሉ የተጠየቁት አቶ ሬድዋን፣ ‹‹አየር መንገዱ እስከሚያውቀው ድረስ የተሟላ ጤንነት እንደነበረው ነው፤›› ብለዋል፡፡
አሶሼትድ ፕሬስ ያነጋገራቸው የረዳት አብራሪ ኃይለመድኅን አጐት መሆናቸውን የሚናገሩት አቶ አለሙ አስማማው የተባሉ ግለሰብ፣ ‹‹ኃይለመድኅን ከቅርብ ወራት ወዲህ በሌላ አንድ አጐቱ ድንገተኛ ሞት ምክንያት ጭንቀት ውስጥ እንደገባ አውቃለሁ፤›› ብለዋል፡፡
‹‹ኃይለመድኅን ዓለም አቀፍ በረራዎች ባሉበት ጊዜያት ሁሉ ጉዞ ከመጀመሩ ቀደም ብሎ ለቅርብ ቤተሰቦቹ ይደውል ነበር፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን መደወል ከማቆሙም በላይ፣ ከቤተሰቦቹም ራሱን እያራቀና አያገለለ መጥቷል፤›› ሲሉ አቶ አለሙ አስረድተዋል፡፡
በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አብሮት መማሩን ለሪፖርተር የገለጸ ስሙን መግለጽ ያልፈለገ አንድ ሰው፣ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ባህር ዳር ጣና ሐይቅ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መማሩንና በ1992 ዓ.ም. ማጠናቀቁን ገልጿል፡፡
በትምህርቱ ጥሩ ውጤት በማምጣትም አዲስ አበባ አራት ኪሎ ዩኒቨርሲቲ ተመድቦ እንደነበር የሚያስታውሰው ይህ ግለሰብ፣ የሥነ ሕንፃ ትምህርት መማር መጀመሩን ነገር ግን ስለማጠናቀቁ እርግጠኛ አለመሆኑን አስረድቷል፡፡
‹‹በኢትዮጵያ አየር መንገድ የፓይለትነት ትምህርት እየወሰደ በነበረበት ወቅት ከመምህሩ ትዕዛዝ ውጪ የመለማመጃ አውሮፕላን በማብረሩ የዲሲፕሊን ዕርምጃ ተወስዶበት ነበር፤›› ሲል አስታውሷል፡፡ ኃይለመድኅን የተወለደው ባህር ዳር ሲሆን፣ አባትና እናቱ እዚያ እንደሚኖሩ አስረድቷል፡፡
ለኢትዮጵያ አየር መንገድ ቅርበት ያላቸው በበኩላቸው ኃይለመድኅን ‹‹በጣም ጐበዝና ተስፋ የሚጣልበት ረዳት አብሪራ ነው፤›› በማለት ይገልጹታል፡፡
ጣሊያናዊ ዜግነት ያላቸው ዋና አብራሪና ረዳት አብራሪ ኃይለመድኅን ባለፈው እሑድ ሌሊት የበረራ ቁጥሩ ‹‹ET 702›› የሆነውን የኢትዮጵያ አየር መንገድ  ቦይንግ 767 አውሮፕላን በማብረር ከ200 በላይ የተለያዩ አገር መንገደኞችን ሮም የማድረስ ኃላፊነትን ከአየር መንገዱ ተረክበዋል፡፡ ይሁን እንጂ ሁለቱ አብራሪዎች በበረራ መቆጣጠሪያ ክፍል (ኮክፒት) ውስጥ የጋራ ቆይታ ያደረጉት የሚያበሩት አውሮፕላን የሱዳን አየር ክልል ውስጥ እስከገባበት ጊዜ ድረስ ብቻ መሆኑ መገለጹ ይታወሳል፡፡
አውሮፕላኑ የሱዳን አየር ክልል ውስጥ በገባበት ወቅት ዋናው አብራሪው መፀጻጃ ቤት ለመሄድ ከበረራ ክፍሉ መውጣታቸውን፣ በዚሁ ወቀትም ረዳት አብራሪው የበረራ ክፍሉን ከውስጥ በመዝጋት ጠለፋውን እንደፈጸመ መዘገቡ እንዲሁ ይታወሳል፡፡
ወደ ሮም ማምራት የነበረበትን አውሮፕላን መስመር በመለወጥ ወደ ስዊዘርላንድ ጄኔቭ ማብረር የቀጠለው ረዳት አብራሪው ኃይለመድኅን፣ የሱዳን አየር ክልል ውስጥ አውሮፕላኑን እንደጠለፈ ለኢትዮጵያ አየር መንገድ ምልክት መስጠቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡ በጄነቭ አውሮፕላን ማረፊያ ክልል ውሰጥ ደርሶ ለሰዓታት በአየር ላይ መቆየቱን የተለያዩ ሚዲያዎች ዘግበዋል፡፡ ሁለት የጣሊያንና አንድ የፈረንሳይ ተዋጊ ጄቶች የተጠለፈውን አውሮፕላን አስገድደው ለማሳረፍ ያደረጉት ሙከራ አለመሳካቱን የውጭ ሚዲያዎች ዘገባ ያመለክታል፡፡
ኃይለመድኅን አውሮፕላኑን ተቆጠጥሮ ወደ ጄኔቭ በሚያመራበት ወቅት ስለተፈጠረው ችግር የሚያውቁ መንገደኞች ጥቂት እንደነበሩ፣ አንዳንዶች ግን ዋና አብራሪው ወደ በሪራ ክፍሉ ለመመለስ የበረራ ክፍሉን በር እየደበደቡ እንዲከፈትላቸው ሲጠይቁት እንደነበር መናገራቸው ተሰምቷል፡፡
በዚህ ጊዜም ረዳት አብራሪው ዋና አብራሪው በሩን መደብደብ ካላቆሙ  አውሮፕላኑን እንደሚከሰከስ በቁጣ መናገሩንና የአደጋ ጊዜ የአየር መሳቢያ ጭንብሎች ከሳጥኖቻቸው ተዘርግፈው ወደ ተሳፊሪዎች እንዲደርሱ እንዳደረገ አንዳንድ ተሳፋሪዎች ተናግረዋል፡፡
በጄኔቭ አውሮፕላን ማረፊያ አካባቢ ሊነጋጋ ሲል የደረሰው  አውሮፕላን በጠላፊው አማካይነት በሰላም ማረፍ የቻለው ከስዊዘርላንድ መንግሥት ባገኘው ፈቃድ መሆኑን አቶ ሬድዋን አረጋግጠው፣ የስዊዘርላንድ መንግሥት ለሰጠው ፈቃድ ምሥጋናቸውን አቅርበዋል፡፡ ግለሰቡ የፖለቲካ ጥገኝነት በስዊዘርላንድ እንዲሰጠው ወይም ለኢትዮጵያ መንግሥት አሳልፈው እንዳይሰጡት መጠየቁን ከሚዲያዎች አንደሰሙ አቶ ሬድዋን ተናግረዋል፡፡
‹‹ጥገኝነት መጠየቁን በተመለከተ ከስዊዘርላንድ መንግሥት መረጃ አልደረሰንም፡፡ ጉዳዩን በተመለከተ የምርመራው ውጤት ሲደርሰን እናሳውቃለን፤›› ሲሉ አቶ ሬድዋን ገልጸዋል፡፡
ጠላፋውን የፈጸመው ረዳት አብራሪ ኃይለመድኅን አበራ የትም አገር መሄድ የሚያስችለው የሙያ ባለቤት መሆኑን የተናገሩት ሚኒስትሩ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ መኖር ካልተመቸው አውሮፕላን መጥለፍ ሳያስፈልገው መሄድ እንደሚችል ጠቁመዋል፡፡
‹‹አውሮፕላን መጥለፍ እዚህ ያለውን አለመመቸት አያካክስም፡፡ እንዲህ ዓይነት ችግር ውሰጥ ሳይገባ ተከብሮ በሥራው ላይ መቀጠል ይችላል፤›› ያሉት አቶ ሬድዋን ግለሰቡ ተላልፎ እንዲሰጥ የኢትዮጵያ መንግሥት ፍላጎት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
ወንጀለኞችን አሳልፎ ስለመስጠት የሚደነግገውን የጄኔቭ ኮንቬንሽን ኢትዮጵያም ሆነ ስዊዘርላንድ ፈርመዋል፣ በመሆኑም ኃይለመድኅን ተላልፎ እንዲሰጥ የሚያስችሉ ሥራዎች እንደሚሠሩ አስረድተዋል፡፡
ረዳት አብራሪ ኃይለመድኅን በአሁኑ ጊዜ በስዊዘርላንድ ፖሊስ ቁጥጥር ሥር ሆኖ ምርመራ እየተደረገበት ሲሆን፣ የስዊዘርላንድ ፖሊስ ዝርዝር መረጃ ከመስጠት ቶቆጥቧል፡፡ ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ዝርዝር መረጃ ለማግኘት የተደረገው ጥረትም አልተሳካም፡፡
Source:  Reporter

No comments:

| Copyright © 2013 Lomiy Blog