ባራክ ሁሴይን ኦባማ: ስለ ማንዴላ

«የማንዴላን አብነታዊነት ማሟላቱ ቢያቅተኝም፥ ምሳሌያዊ ምግባራቸዉ የተሻለ ሰዉ ለመሆን እንድጥር ያበረታታኛል።» ባራክ ሁሴይን ኦባማ፥ የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት። ታሕሳስ 1/ 2006

ቀኑ ዝናባማ ቢሆንም ከ80 000 በላይ ህዝብ በሲዮቶው የዓለም ዋንጫ ስታዲየም በተካሄደው ስነስርዓት ላይ መገኘቱ ታውቐል።
የማንዴላ የቀብር ስንስርዓት የፊታችን እሁድ የትውልድ መንደራቸው በሆነችው የኩኑ ቀበሌ ይፈጸማል ተብሎ ይጠበቃል።

የኔልሰን ማንዴላ የኣሸኛኘት ስነስርዓት የተካሄደው በጆሃንስበርግ ከተማ ስዌቶ በሚገኘው የዓለም ዋንጫ ስታዲየም ነበር። ዕለቱ ከማለዳው ጀምሮ ዝናባማ ቢሆንም ከጆሃንስበርግ ከተማ እና ከተለያዩ የኣገሪቱ ከተሞች የመጡ ታዳሚዎች ከረፋዱ ጀምሮ ነበር በስታዲየሙ ዙሪያ የተሰባሰቡት። ቀትር
ላይ ሲከፈት በትንሹ 80 000 ያህል ታዳሚዎች በስታዲየሙ ተገኝቷል። ከተለያዩ የዓለም አካባቢዎች የመጡ የመንግስታት መሪዎች፣ የኃይማኖት ዓባቶች፤ ታዋቂ ግለሰቦችና በርካታ የዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብ ተጠሪዎችም ተሳትፏል። ከ70 በላይ የኣገር መሪዎችም በስነስርዓቱ ላይ ታድሟል። የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ ከባለቤታቸው ሚሼል ኦባማ እና ከቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ጆርጅ ቡሽ ጋር በመሆን ዛሬ ማለዳ ነበር ጆኃንስበርግ የገቡት። ሁለቱ የቀድሞ ፕሬዝደንቶች ቢል ክሊንተን እና ጂሚ ካርተርም ለየብቻቸው ጆኃንስበርግ ገብተው በስነስርዓቱ ላይ ነበሩ። የተመድ ዋ/ጸኃፊ ባንኪሙንን ጨምሮ የኣፍሪካ ህብረት ኮሚሺን ሊቀመንበሯ ዶ/ር ዲላሚኒዙማ እና ሌሎች ከፍተኛ ባለስልጣናትም ተገኝቷል። የማንዴላ ባለቤት ግሬሳ ሚሼል በቤተሰብ አባላት ታጅበው ወደስታዲየሙ ሲገቡ ሞቅ ያለ ኣቀባበል ነበር የተደረገላቸው። የማንዴላ የቀድሞው ባለቤት ዊኒ ማንዴላም በስፍራው ነበሩ።

ስነስራዓቱ የተጀመረው የደቡብ ኣፍሪካን ብሄራዊ መዝሙር በመዘመር ነበር። ቀጥሎም እስልምናን ጨምሮ የክርስትና የኣይሁድ እና የሌሎች እምነቶች ተከታዮችም እንደየ ኃይማኖቶቻቸው ጸሎት ኣድርገዋል። እያንዳንዱ ተናጋሪ የማንዴላን ህይወትና ውርስ በማወደስ ወደር የማይገኝላቸው ታላቅ መሪ እንደነበሩ ሲመሰክሩ ውሏል። የተመድ ዋና ጸኃፊ ባንኪሙን ዓለም በተይም ኣፍሪካ ኣሁን ባለችበት ደረጃ ለመቆም ማንዴላ ያበረከቱት ድርሻ በቀላሉ የሚገመት ኣይደለም ሲሉ ምስክርነታቸውን ሰቷል።
የዛሬ 30 ዓመት ገደማ ነበር በት/ቤት ስለ ማንዴላ የተማርኩት በማለት የጀመሩት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ ከማንዴላ የተማርናቸው የላቁ ብቃቶችን ልንጠቀምበት ይገባል ሲሉም ኣክሏል። በኣሁኑ ሳዓት ስለተናገሩ፣ ስለጻፉና ስላሰቡ ጭምር ለእስራት የተዳረጉ በርካታ ዜጎች በዓለም ዙሪያ ይገኛሉ ያሉት ኦባማ የደቡብ ኣፍሪካ ህዝብ ማንዴላን ስላበረከታችሁልን የዓለም ህብረተሰብ ያመሰግናቿል ብሏል።
ባራክ ኦባማ በዚህ ኣጋጣሚ በቀዝቃዛው ጦርነት ወቅት ለዘመናት ምናልባትም ኣሁንም ድረስ የመንግስታቸው ባላንጣ ከሆኑት የኪዩባው መሪ ራውል ካስትሮ ጋርም እጅ ለእጅ ሲጨባበጡ ያስተዋሉ በርካታ ታዛቢዎች ማንዴላ ሞተውም የይቅርታና የእርቅ መንፈስ መሆናቸውን ያመለክታል ሲሉ ተደምጧል።
የኢራን እና የብራዚል ፕሬዝደንቶችም የማንዴላን ውርስና ቅርስ እንዲዘክሩ ከተመረጡት መካከል ናቸው። ኣፍሪካም በናይጄሪያው ፕሬዝደንት ጉድላክ ጆናታን ተወክላለች። የዛሬው የኣሸኛኘት ስነስርዓትም የፊታችን እሁድ የሚፈጸመው የቀብር ስነስርዓት አካል ነው ተብሏል።
ማንዴላ የሚቀበሩት በምስራቅ ኬፕ ክ/ሀገር በምትገኘው እና ኩኑ ተብላ በምትታወቀው ገጠራማ የትውልድ መንደራቸው እንደሆነም ታውቐል። ከዛሬው ስነስርዓት በኃላ ኣስክሬናቸው በቀጥታ የቀድሞው የነጮች ኣገዛዝ መቀመጫ ወደነበረው የፕሪቶሪያ ቤተመንግስት ተወስዷል። ለሚቀጥሉት ሶስት ቀናትም በዚያው ለተሰናባቾች ክፍት ሆኖ ይቆያል ተብሏል። ህንጻው ማንዴላ ለፕሬዝደንትነት እንደተመረጡ ቃለ መሀላ የፈጸሙበት ሲሆን ከዚህ በኃላ በእሳቸው ስም እንዲሰየምም ተወስኗል።
የደቡብ ኣፍሪካው ፕሬዝደንት ያቆብ ዙማም የማንዴላን ህያው ተግባራት በማወደስና ቤተሰባቸውን በማጽናናት ነበር ንግግራቸውን የጀመሩት። ወዲያውኑ ግን ከታዳሚው ከፍተኛ ጩሀት ኣስተጋባ። ተቃውሞ መሆኑ ነው። ለደቂቃዎች ያህል ንግግራቸውን ለማቐረጥም ተገደዱ። ዘገባዎች እንደሚያመለክቱት ዙማ በሙስናና በብልሹ ኣስተዳደር መተቸት ከጀመሩ ሰነባብቷል።
ነገ ማክሰኞ ደግሞ በኣጋጣሚ የመጀመሪያው የደቡብ ኣፍሪካ ጥቁር ፕሬዝደንት ኔልሰን ማንዴላና የመጨረሻው ነጭ የኣገሪቱ ፕሬዝደንት ፍሬድሪክ ዴክለርክ የሰላም የኖቤል ሽልማት የተሸለሙበት ልክ 20ኛ ዓመቱ።
ጃፈር ዓሊ
ነጋሽ መሀመድ
Source: ww.dw.de
 

No comments:

| Copyright © 2013 Lomiy Blog