የማንዴላ አሰተምሕሮ እና ድሕረ-ማንዴላ

ፍልስጤም-እስራኤሎች፥ ዋሽንግተን፥ ሞስኮዎች፥ ዋሽንግተን፥ ቤጂንግ፥ ዋሽንግተን ቴሕራኖች፥ ዋሽንግተን ሐቫናዎች፥ አስመራ-አዲስ አበቦች፥ ኢሕአዲግ ተቃዋሚዎች፥ ሶማሌዎች፥ ሶሪያዎች፥ ብዙ ናቸዉ። ቁጥራቸዉን መዘርዘሩ ያታክታልም። ከማንዴላ ምግባር ጥቁቱን፥ ከዴክላክ ድፍረት ትንሹን እንኳን ገቢር አለማድረጋቸዉ በርግጥ ያጠያይቃል 
ማንዴላ ተቀበሩ። ታላቁ የነፃነት፣ የእኩልነት አርበኛ ከሞቱበት እስከ ተቀበሩበት ድፍን ዓለም አዘነ፥ ወይም ማዘኑን ገለፀ። ከቄሱ እስከ ሼኩ፥ ከዘማሪዉ እስከ ዘፋኙ፥ ከተዋኙ እስከ ስፖርተኛዉ ለዚያ ታላቅ-ክቡር ሠዉ ታላቅ አድናቆት፥ አክብሮቱን ሲያንቆረቁር ሰነበተ። ከፕሬዝዳት ዙማ-እስከ ፕሬዝደንት ኦቦባ፥ ከጠቅላይ ሚንስትር ኃይለ ማርያም እስከ ጠቅላይ ሚንስትር ካሜሩን የትንሽ ትልቁ ሀገር መሪ የማንዴላን አብነት ለመከተል፥ ዓላማ፥ ራዕይ አስተምሕሯቸዉን ገቢር ለማድረግ ቃል ገባ። ካንጀት-ይሆን ካንገት ማረጋገጪያዉ-በያኙ በርግጥ ምግባር እና ጊዜ ነዉ። ማንዴላ
ፈጥራ በማንዴላ የተፈጠረችዉ ራስዋ-ደቡብ አፍሪቃ ግን በማንዴላነቷ መቀጠሏ ካሁኑ አያነጋገረ ነዉ። ብልጭ ያሉ፥ እዉነት፥ አስተያየቶቾን እያጠቃቀስን ላፍታ አብረን እንቆዝም።

ባለፈዉ ማክሰኞ፥ ለማንዴላ የሐዘን ስንብት ድግሥ በታደመዉ ሕዝብ መሐል፥ የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝደንት ባራክ ኦቦማ የኩባ አቻቸዉን ራዑል ካስትሮን መጨበጣቸዉ ማንዴላ ሞተዉም ጠላቶችን ያጨባበጡ፥ ጉደኛ ሰዉ አሰኝቶ ነበር። እያሰኘም ነዉ። ይሁንና ኦባማ-ከፖለቲካ መርሕ አብነታቸዉ ከክሊንተን፥ ራዑል ከትግል ጓድ፥ ከስልጣን ርዕዮተ-ዓለም፥ አዉራሻቸዉ፥ ከሁሉም በላይ ከታላቅ ወንድማቸዉ ከፊደል የተለየ ነገር አላደረጉም።

መስከረም 8 ሁለት ሺሕ (ዘመኑ በሙሉ እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር ነዉ።) የያኔዎቹ የሁለቱ ሃገራት መሪዎች ቢል ክሊንተን እና ፊደል ካስትሮ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጉባኤ ላይ ተጨባብጠዉ ነበር። ያኔም እንዳሁኑ በርግጥ ጉድ ተብሎ ነበር። እና አሁን ጉድ ካሰኘ-ጉድ ማሰኘት የነበረ-ያለበት፥ የሚኖርበትም የዓለም አቻ የለሽ ግዙፍ፥ ኃያል፥ ሀብታም ሀገር ከትንሽ፥ ደሀ፥ ደካማይቱ ደሴት ጎረቤቷ ጋር ለስልሳ ዘመናት በጠላትነት መፈላለጓ በሆነ ነበር።

ጉድ ካሰኛ የትልቂቱ ሀገር የመጀመሪያ የጥቁር-ነጭ ክልስ መሪ የማንዴላን አብነት ገቢር ማድረግ እንደማይችሉ ባደባባይ ማመናቸዉ ጉድ ባሰኘ ነበር።


«ኔልሰን ማንዴላን ብጤ ከእንግዲሕ ብጨራሽ አናገኝም። ይሁንና ለአፍሪቃ እና ለመላዉ ዓለም ወጣቶች የሚከተለዉን ልናገር፥-የማንዴላን የሕይወት ምግባር የራሳችሁ ማድረግ ትችላላችሁ። ከሠላሳ ዓመት በፊት ገና ተማሪ እያለሁ ስለማንዴላ እና እዚች ሀገር ስለሚደረገዉ ትግል ተምሬያለሁ። ይሕ በዉስጤ የሆነ ነገር አጭሯል። ለሌሎች እና ለራሴ ኃላፊነት እንዳለብኝ ቀስቅሶኛል። እና ዛሬ ከዚሕ ካደረሰኝ አስቸጋሪ ጉዞ ዶሎኛል። የማዲባን አብነታዊ ምሳሌ ገቢር ለማድረግ ቢያቅተኝም የተሻለ ሠዉ ለመሆን እንድጥር አድርጎኛል።»

ማንዴላ ተወንጅለዉ፥ ታስረዉ፥ የጠላቶቻቸዉን ቋንቋ ተምረዉ፥ ተፈተዉ፥ ለጠላቶቻቸዉ ይቅር ብለዉ ደቡብ አፍሪቃን ዴሞክራሲያዊት ደቡብ አፍሪቃን ፈጥረዉ፣ መርተዉ፣ ኖረዉ ሞቱ። የዓለም ፖለቲከኞች እንዳሉና እንደሚሉት የዓለም የትንሹም የትልቁም አብነት ናቸዉ። በተለይ ለአፍሪቃ -የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚንስትር እና የወቅቱ የአፍሪቃ ሕብረት ሊቀመንበር አቶ ኃይለ ማሪያም ደሳለኝ እንዳሉት የወደፊት ተስፋዋም አብነት ናቸዉ።

«እንደ የአፍሪቃ ብሔራዊ ምክር ቤት እዉነተኛ መሪ እና ልዩ ሰብዕናቸዉ ሁሉ፥ የማንዴላ ሕይወት የክፍለ-አሐጉሪቱን የወደፊት (ተስፋ) የሚወክልም ነዉ።»

ጠቅላይ ሚንስትር ኃይለማርያም ከአዲስ አበባ ወደ ቁኑ ከመብረራቸዉ በፊት-አርብ፥ ከዚያዉ ከአዲስ አበባ ይሕን ሰምተን ነበር።

ፍልስጤም-እስራኤሎች፥ ዋሽንግተን፥ ሞስኮዎች፥ ዋሽንግተን፥ ቤጂንግ፥ ዋሽንግተን ቴሕራኖች፥ ዋሽንግተን ሐቫናዎች፥ አስመራ-አዲስ አበቦች፥ ኢሕአዲግ ተቃዋሚዎች፥ ሶማሌዎች፥ ሶሪያዎች፥ ብዙ ናቸዉ። ቁጥራቸዉን መዘርዘሩ ያታክታልም። ከማንዴላ ምግባር ጥቁቱን፥ ከዴክላክ ድፍረት ትንሹን እንኳን ገቢር አለማድረጋቸዉ በርግጥ ያጠያይቃል። አጠያየቀም አላጠያየቀ ኦባማ እንዳሉት ማለትና-ማድረግ ለየቅል፥ አንዳንዴም ተቃራኒ ናቸዉ።

«ስለዚሕ እኛም ለፍትሕ (ሥርፀት)፥ ለሰላም (ፅናት) እርምጃ መዉሰድ አለብን። የማዲባን በዘር መካካል እርቅ የማዉረድ ዉርስ-ቅርስን በደስታ የሚቀበሉ፥ ግን በተቃራኒዉ ሥር የሠደደ ድሕነትን፥የኑሮ ተባለጥ ለመቋቋም፥ መጠነኛ ለዉጥ ማድረግን እንኳን ከልባቸዉ የሚቃወሙ በርካታ ሰዎች አሉ።»

ማንዴላ እራሳቸዉ ደጋግመዉ እንዳሉት ተዓምረኛም፥ ቅዱስም አይደሉም። ብዙዎች እንደመሠከሩት ግን አንድ ሰዉ ሊያደርገዉ ከሚገባዉ በላይ አድርገዉ፥ ዴሞክራሲያዊት ደቡብ አፍሪቃን ፈጥረዉ እንደ አንድ ሰዉ አረፉ፥ አለፉ። የማንዴላ ደቀመዛሙርት፥ የርዕዮተ-ዓለም፥ የሥልጣን ወራሾች እንደተቀረዉ ዓለም መሪዎች ሁሉ የማንዴላን ጅምር ለመቀጠል፥ ራዕይ-አስተምህሯቸዉን ገቢር ለማድረግ ቃል ገብተዋል።

«(ማዲባ) በህይወታችን ከአንድ መሪ የምንፈልገዉና ሊኖረን የሚገባዉ መሪ ሆነህ በአስቸጋሪ ወቅት በመገኘትህ እናመሰግናለን። ለነፃነት የተደረገዉ ረጅም አካላዊ ጉዞ ቢያበቃም፥ የኛ የራሳችን ጉዞ ግን ይቀጥላል። አበክረሕ የጣርክለትን ዓይነት ማሕበረሰብ ለመመሥረት በጀመርከዉ መቀጠል አለብን። ጅምርህን ወደፊት ማራመድ አለብን። ከበለፀገዉ ልዩ ምግባርህና ከሕይወት ልምድህ መማራችንን እንቀጥላለን።»

ፕሬዝደንት ጄኮብ ዙማ። ዕሁድ። የማንዴላዋ ዴሞክራሲያዊት ደቡብ አፍሪቃ በ1994 ስትመሠረት በምጣኔ ሀብት ዕድገት የነበራትን ሥፍራ ዛሬም አለቀቀችም። ከአፍሪቃ አንደኛ ናት። ከአፍሪቃ አጠቃላይ ዓመታዊ ገቢ ሃያ-አራት በመቶዉን ትይዛለች። ማንዴላ ሲፈጥሯት ትንሽ የነበረዉ ሙስና ግን ዛሬ ሰንጎ ይዟታል።

የማንዴላን ፅናት፥ ሥልት፥ የአስተዳደር አመራር ብልሐትን ለመቀጠል ቃል የገቡት ፕሬዝደንት ዙማ ራሳቸዉ በመንግሥት ገንዘብ በሃያ-ሁለት ሚሊዮን ዶላር መኖሪያ ቤት ማስገንባታቸዉ በሰፊዉ እየተነገረ ነዉ። ዙማ ቤቱን ከቤተሰባቸዉ በተሰጣቸዉ ገንዘብ ማስገንባታቸዉን መናገራቸዉ አልቀረም። ያመናቸዉ ግን የለም።

ማንዴላ ሁሉንም ዘር ያሳተፈ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት በመሠረቱበት ወቅት የደቡብ አፍሪቃዊዉ ሥራ አጥ ቁጥር አስራ-ስድስት በመቶ ነበር። ዘንድሮ ግን ከአንድ አራተኛ የሚበልጠዉ ደቡብ አፍሪቃዊ ሥራ የለዉም። ሃያ-አምስት ከመቶ። በዚሕ ቁጥር ላይ ሥራ መፈለግ ያቆመዉ ሁለት ሚሊዮን ያህል ሕዝብ ሲጨመርበት የሥራ-አጡ ቁጥር ሠላሳ ሰባት ከመቶ ሊደርስ ይችላል።


የሠራተኞች ተደጋጋሚ የሥራ ማቆም አድማ፥ የባለሥልጣናት ሙስና፥ የግልፅ የምጣኔ ሀብት መርሕ ችግር ከዓለም የምጣኔ ሀብት ክስረት ጋር ተዳምሮ የአፍሪቃዋ የምጣኔ ሀብት ቋት ምጣኔ ሀብታዊ ዕድገት በእጅጉ እያዘገመ ነዉ። የአብዛኞቹ የአፍሪቃ ሃገራት ምጣኔ ሀብት ከአምስት-እስከ ሰባት ከመቶ በሚያድግበት በዚሕ ዘመን የደቡብ አፍሪቃ አማካይ የምጣኔ ሀብት ዕድገት 3.5 ከመቶ ላይ ያጣጥራል።

ከማንዴላ በፊት የሠላም ኖቤልን የተሸለሙት ቄስ ዴዝሞንድ ቱቱ የማንዴላ ጅምር ዳር እንደሚዘልቅ፥ የሐገራቸዉ የወደፊት ጉዞ እንደሚሰምርም ይናገራሉ።

«አባታችን ሞተ፥ ከእንግዲህ ምን ይገጥመናል? ሞቱ የምፅዓት ቀንን እና ጥፋትን ያስከትልብን ይሆን? አንዳንዶች እሱ አሁን እንዳለፈዉ ካለፈ በኋላ ሀገራችን ትነዳለች ይላሉ። ይሕ እንደሚመስለኝ እኛን ደቡብ አፍሪቃዉያንን አሳንሶ መመልከት ነዉ። የእሱን ቅርስ ማሳነስ ነዉ። ጀምበሯ ነገም ተወጣለች፥ ከነገወዲያ፥ በሚቀጥለዉ ቀንም። እንደ ትናንቱ ደማቅ አትሆን ይሆናል፥ ሕይወት ግን ይቀጥላል።»

እንደመንፈሳዊ አባት መጪዉን ዘመን በበጎ ተስፋ ከመቃኘት፥ ጥሩ ጥሩዉን ከመስበክ ሌላ-ሌላ ማለት በርግጥ የቄስ ምግባር አይደለም። ቱቱ እንዳሉት ሕይወት ደብዛዛም ቢሆን ይቀጥላል። ጥናቶች እንደሚጠቁሙት ከደቡብ አፍሪቃ ጥቁሮች ስልሳ ሁለት በመቶ ለሚሆኑት የነዙማ መንግሥት ፈጣን መፍትሔ ካለመጣላቸዉ ሕይወታቸዉ የሚቀጥለዉ ከድሕነት ጠገግ በታች እየማቀቁ ነዉ።

ፖለቲካዉም ከኤኮኖሚዉ የተለየ አይደለም። ከ1994 ጀምሮ ደቡብ አፍሪቃ ያለ ብዙ ተቀናቃኝ የሚመራዉ የደቡብ አፍሪቃ የአፍሪቃ ብሔራዊ ምክር ቤት (ኤ.ኤን.ሲ) በመሪዎቹ ሽኩቻ፥ መጠላለፍና ሙስና ግራ ቀኝ እየተላጋ ነዉ። ANC በሁለት ሺሕ አራት በተደረገዉ ምርጫ ሰባ ከመቶ ያህል ድምፅ አግኝቶ ነበር። ከአምስት አመት በሕዋላ በተደረገዉ ምርጫ ግን ANC ያገኘዉ ድምፅ ስልሳ፥ ስድስት ከመቶ እንኳን አይሞላም።

በመጪዉ ዓመትም ምርጫ አለ።2014 እርግጥ ነዉ የዙማ እና የኢምቤኪ (የቀድሞዉ ፕሬዝዳት) ደጋፊ በሚል በሁለት የተከፈሉት የፓርቲዉ አባላት ንትርክ ቀዝቀዝ ያለ መስሏል። ይሁንና ምርጫዉ የሚደረገዉ አድማ በመቱ የማዕድን ቆፋሪዎች ላይ በተፈፀመዉ ግድያ ሰበብ እስካሁን ለኤ.ኤን ሲ ያላሰለሰ ድጋፍ ሲሰጡ የነበሩት የሠራተኞች ማሕበራት መሪዎች ከፓርቲዉ መሪዎች ጋር በሚወዛገቡበት ወቅት ነዉ።

የቀድሞዋ የፀረ-አፓርታይድ እዉቅ ታጋይ ዶክተር ማምፌሌ ራምፌሌ ለረጅም ጊዜ ከሚደግፉት ከኤ.ኤን ሲ አፈንግጠዉ ባለፈዉ የካቲት የራሳቸዉን ፓርቲ መስርተዋል። የኤ.ኤ.ን ሲን የወጣቶች ክንፍ ይመሩ የነበሩት ጁሊየስ ማሌማም ከፓርቲዉ ከተባረሩ በኋላ ባለፈዉ ጥቅምት አዲስ ፓርቲ መስርተዋል።

የአንጋፋዉ ፓርቲ መሰነጣጠቅ ነጮች ለሚበዙበት ለዋነኛዉ ተቃዋሚ ፓርቲ ለዴሞክራቲክ ሕብረት ጥሩ አጋጣሚ ነዉ። እየተራበ፥ እየተቸገረ፥ መሪዎቹ በስሙ በያዙት ሥልጣን እንደሚቀማጠሉ እያወቀ የማንዴላ ሥም፥ ግርማ ሞገስ፥ የገድል-ድላቸዉ ዝና ብቻ ትዕግስት ሆኖት የቆየዉ ሕዝብ እስካሁን በታገሰበት መንገድ መታገሱ አጠራጣሪ ነዉ። እሳቸዉ ደግሞ ይሰጋሉ።ነጭ ናቸዉ።ደቡብ አፍሪቃዊት።

«ያሰጋኛል። ምክንያቱም፥ እንደሚመስለኝ ይህ የአንድ ዘመን ፍፃሜ ነዉ። ነጮች እና ጥቁሮች አብረን የኖርንበት ዘመን ፍፃሜ እንዳይሆን እፈራለሁ። ብዙ መጥፎ ሰዎች እሳቸዉን (ማንዴላን) ስለሚያከብሩ ብቻ መጥፎ ነገር ከማድረግ የታቀቡ ይመስለኛል። እነዚሕ ሰዎች ይህቺን ሀገር ምናልባት ወደ ሌላ አቅጣጫ ይነዷታል ብዬ እሰጋለሁ።»

ሰዉዬዉ፥ በ1962 ከደቡብ አፍሪቃን በሕገ-ወጥ መንገድ በመዉጣት እና የሥራ ማቆም አድማን በማነሳሳት በተከሰሱ ወቅት፥ ከሳሹ አቃቤ ሕግ ፒ.ጄ ቡሽ ይባሉ ነበር። አቃቤ ሕጉ ነጭ እና የነጭ ዘረኞቹ መንግሥት አቀንቃኝ ናቸዉ። ማንዴላ ላይ ሊፈረድ ሲል «አንዴ ለብቻዉ ላነጋግረዉ እፈልጋለሁ» ይላሉ አቃቤ-ሕጉ። ተፈቀደላቸዉ። ማንዴላን ጨበጧቸዉ አሏቸዉም «መልካሙን ሁሉ እመኝልሃለሁ።» ለሳቸዉ የሰላም እረፍት፥ ለናንተ መልካም ጊዜ ልመኝ። እና እንደተለመደዉ ስለ ማሕደረ ዜና አስተያየታችሁን፥ በደብዳቤ፥ በስልክ፥ በኢሜይል፥ በፌስ ቡኩም እንድትሰጡ ጠይቄ ልሰናበት። ነጋሽ መሐመድ ነኝ ቸር ያሰማን።
ነጋሽ መሐመድ
ሸዋዬ ለገሠ
Source: www.dw.de
 

No comments:

| Copyright © 2013 Lomiy Blog