የምግብ እጥረትና ብክነት

ዓለም የምግብ እና የእርሻ ድርጅት በዓለማችን ከስምንት መቶ ሚሊዮን በላይ ሕዝብ እየተራበ የሚታየዉ የምግብ ብክነት ተቀባይነት እንደሌለዉ አመለከተ። ድርጅቱ ዛሬ ይፋ ባደረገዉ ዘገባዉ የምግብ ማጣት ብቻ ሳይሆን የተመጣጠነና በቂ ምግብ አለማግኘት አካላዊ እድገታቸዉ ለእድሜያቸዉ የማይመጥን ልጆች ቁጥርም 165 ሚሊዮን መድረሱንም አስታዉቋል።
ኢትዮጵያ ዉስጥ ያለፈዉ ዓመት የመኸር ዝናብ መጠንና ስርጭት የተሻለ ምርት እንደሚገኝ ተስፋ አሳድሯል። የምግብ ርዳታ የሚጠብቀዉም ሶስት ሚሊዮን አይሞላም።
በዓለማችን በአንድ ወገን የተትረፈረፈ ምግብ እየተመረተ ለብክነት ሲዳረግ በሌላዉ በኩል ደግሞ የዕለት ጉርስ የሚሻዉ ወገን በረሃብ አንጀቱ መታጠፉ አግባብነት የለዉም ይላል የዓለም የምግብና የእርሻ ድርጅት ማለትም FAO። እንድርጅቱ ዘገባ ከሆነም በየዓመቱ በዓለም ከሚመረተዉ የምግብ እህል አንድ ሶስተኛ እጁ ማለትም 1,3 ቢሊዮን ቶን ከተራቡት ጉሮሮ የሚገባ ሳይሆን እንደቆሻሻ የሚጣል ነዉ። በዓለም ወደሁለት ቢሊዮን ሰዎችም ለጤና እጅግ ጠቃሚ የሆኑ የቪታሚንና የማዕድናት እጥረት ተጎጂም እንደሆኑ FAO ዘገባዉ ያመለከተዉ።
ለምግብ ብክነቱ የዝናብ እጥረትና ድርቅ ሁኔታ በሚያስከትለዉ ተጽዕኖ የሚበላዉ መጥፋት ብቻ ሳይሆን እንደየአካባቢዉ የአመጋገብ ልማድም ለምግብነት የማይዉሉ መኖራቸዉ ችግሩን ማባባሱ ነዉ የተገለጸዉ። FAO እንደሚለዉ ለምሳሌ ኢትዮጵያ ዉስጥ የፍየል ርባታ ላይ ያተኮረዉ ፕሮጀክት የወተት ፍጆታንና በእሱም የሚገኘዉን ገቢ በብዛት ጥቅም ላይ ማዋል አስችሏል።
ያም ሆኖ ግን እንዲህ ዓይነት ፕሮጀክቶች ዓለም ዓቀፍ ድጋፍ የሚሹ መሆናቸዉን ድርጅቱ አስታዉቋል። የኢትዮጵያ ግብርና ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴታ አቶ ምትኩ ካሣ የምግብ ለሥራ አገልግሎት በመኖሩና የተረጂም ቁጥር በመቀነሱ ሀገሪቱ ዘንድሮ ብዙም የምግብ እርዳታ የምትጠብቅበት ደረጃ ላይ እንዳልሆነች ገልጸዋል። እንዲያም ሆኖ ግን አሁንም በአርብቶ አደሩ አካባቢ ችግሩ መኖሩን አመልክተዋል።
ርዳታ የሚያስፈልጋቸዉ ወገኖች በተገቢዉ ጊዜና መጠን የምግብ ድጋፍ እንደሚያገኝ ያመለከቱት የግብርና ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴታ ረድኤቱ ከሀገር ዉስጥም ከዉጭም እንደሚገኝም ገልጸዋል። በአርብቶ አደሩ አካባቢ የዝናብ እጥረት እና ከአኗኗር ይትበሃል አኳያ የምግብ ርዳታዉ መኖሩን ቢገልጹም ርዳታዉ ጊዜያዊ መፍትሄ እንጂ ዘላቂ ለዉጥ አያመጣምና ያንን ለመለወጥ የተጀመሩ እቅዶች ተግባራዊ እየሆኑ መሆናቸዉንም አቶ ምትኩ ያስረዳሉ።
በተመሳሳይ በኦሮሚያ ክልል በዝናብ አጠር አካባቢዎች እንዲሁም በተለያዩ አደጋዎች ምክንያት ለችግር ተጋልጠዉ የምግብ ርዳታ የሚያስፈልጋቸዉ ወገኖች መኖራቸዉን የክልሉ ግብርና ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነት አቶ አበራ ለማ አርሶ አደሮቹ ከዚህ ሁኔታ የሚወጡበት አቅጣጫ ተይዞ እየተሠራ ነዉ ይላሉ። እርዳታዉም ሥራ ሠርተዉ በምግብ መልክ፤ አለያም በገንዘብ ብድር የሚሰጣቸዉ መሆናቸዉንም ዘርዝረዋል። የዘንድሮዉ የዝናብ ሁኔታ ጥሩ እንደነበር በማመልከትም የተሻለ ምርት እንደሚጠበቅ ነዉ ሁለቱም የሚያመለክቱት።
ሸዋዬ ለገሠ
አርያም ተክሌ
Source: www.dw.de
 

No comments:

| Copyright © 2013 Lomiy Blog