የፕሮፌሰር ጌታቸው ነገር! (ወርቁ ፈረደ)

ብሄርተኝነትን ታጥቀው አገራችንን ወደ አደገኛ ጠርዝ ከሚገፏት ምሁራን መካከል፣ የተወሰኑት ላይ የአቅሜን ያህል ሂስ ለመሰንዘር ሞክሬያለሁ፡፡ አሁን ደግሞ የፕሮፌሰር ጌታቸውን አንዳንድ የተዛቡ ሀሳቦች ለመዳሰስ እሞክራለሁ፡፡
ፕሮፌሰር ጌታቸው አንቱ የሚባሉ ምሁርና አንተ የሚባሉ ፖለቲከኛ ናቸው፡፡ ጥናቶቻቸውን አንብቦ በእውቀታቸው ስፋት እና በጽሁፍ ችሎታቸው የማይደነቅ ሰው ማግኘት ይከብዳል፡፡ ያም ሆኖ ጌቾ በመጣጥፎቻቸው፣ በግለ ታሪካቸው፣ እንዲሁም የአባ ባህርይ ድርሰቶችን በሰበሰቡበትና ባሰናዱበት ጥራዛቸው የሚያንጸባርቋቸው አንዳንድ የተዛቡና አደገኛ ሐሳቦች አብረው የሚያኗኑሩ አይደሉም:፡
ለምሳሌ በቅርቡ፣ በአንዳንድ የኦሮሞ ብሄርተኞች በኩል ለሚሰነዘሩ ዘለፋዎች ምላሽ እንዲሆን የጻፉትን “ዕርቅና ሰላም፣ የሕይወት ቅመም” የተባለ መጣጥፋቸውን ያነበበ ሰው፤ አንጋፋ ምሁራኖቻችን ከዕርቅና ከሰላም ጋራ እንዴት አድርገው እንዳቆራረጡን መረዳት አያቅተውም፡፡
ጌቾ፣ ለአገሪቱ ቅርስ ውድመት የእስልምና እምነትና የኦሮምኛ ተናጋሪ ጎሳዎችን ተጠያቂ አድርገዋል፡፡ እርግጥ ነው፣ የግራኝ አህመድ ጦር ወደ መሀል አገር በዘመተ ጊዜ እንዲሁም የኦሮሞ ገዳ ጦር አንዳንድ የአገሪቱን ክፍሎች በጦር ባስገበረ ጊዜ አያሌ ሰብአዊ፣ ቁሳዊና መንፈሳዊ ሀብቶች ላይ ውድመት መድረሱ የተረጋገጠ ነው፡፡

ይሁን እንጂ አውዳሚነትን ከአንድ ብሄረሰብ እና ከአንድ ሀይማኖት ጋር አያይዞ ማቅረብ አድልኦ እንጂ እውቀት ሊሆን አይችልም፡፡ ዋናው የውድመት ምንጭ ሁሉም ብሄረሰቦችና ሁሉም ሀይማኖቶች የሚጋሩት የጦርነት ባህላችን ነው፡፡ በጦርነት ወቅት ክርስትያን ነገስታትም ቤተ-ክርስትያን አቃጥለዋል፡፡ ቅርስ በዝብዘዋል፡፡ ለምሳሌ፣ አለቃ ወልደማርያም በጻፉት ዜናመዋእል ውስጥ በጎንደር ስለተካሄደ አንድ ጦርነት ሲዘግቡ “(ቴዎድሮስ) በጎንደር ቤተክርስትያን በከተማው ውስጥ ያለውን አቃጠሉ፡፡ ከከተማው የራቀው ግን በእግዜር ትእዛዝ ተረፈ” ይላሉ፡፡
ቴዎድሮስ እና አብዛኞቹ ወታደሮቻቸው የኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ነበሩ፡፡ ነገር ግን ኦርቶዶክስነታቸው፣ ከሙስሊሙ ወይም ከአገር-በቀል እምነት ተከታዩ የተሻለ ለቅርስ እንዲራሩ አላደረጋቸውም፡፡ ስለዚህ አንዱን እምነት በቅርስ ፈጣሪነት፣ ሌላውን በቅርስ አውዳሚነት መፈረጅ ኢ-ታሪካዊ ይመስለኛል፡፡
ፕሮፌሰሩ በብሄረሰቦች ጥናት ላይ ያላቸውን እውቀት ለማዋጣት ደክመዋል፡፡ ይሁን እንጂ እውቀታቸው በፍርዳቸው ሲበላሽ እናያለን፡፡ የትግራይ ብሄር ተወላጆችን ሳያስቆጡ ስለ ትግራይ፣ የኦሮሞ ተወላጆችን ሳያስቆጡ ስለ ኦሮሞ መናገር ያቅታቸዋል፡፡ ለምሳሌ በአባ ባህርይ መጽሐፋቸው፣ ኦሮሞ የሚለውን መጠርያ በነውረኝነት ከሚጠቀሰው መጠርያ በኋላ የመጣ አስመስለው ለማሳመን ሞክረዋል፡፡ ያ ቃል ከጥንት የኖረ ለመሆኑ ጥንታውያን ጸሐፊዎቹን እነ አባ ባህርይን፣ አለቃ አጥሜንና አለቃ ታዬን በዋቢነት ይጠቅሳሉ፡፡
ምክንያታቸው ምንም ይሁን የተጠቀሱት ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት በኦሮሞ ጥናት ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን መጽሀፋቸውን ያነበበ ሁሉ የሚረዳው ነው፡፡ ይሁን እንጂ ከአድልኦ የነጹ አልነበሩም፡፡ የሚበይኑት ብያኔ፣ የሚጠቀሙት ስያሜ ሁሉ በባእድ አስተያየት የተቃኘ ነው፡፡ በሌላ በኩል፣ በዘመነ መሳፍንት ማክተሚያ ላይ በኦሮሞ መካከል ኖሮ፣ የመስክ ጥናት ያካሄደው አንቶኒዮ ደ አባዲ ኦሮሞዎች ራሳቸውን ኦሮሞ ብለው እንደሚጠሩ ጽፏል፡፡ “የኢትዮጵያ ጂኦግራፊ” በተባለው ስራው ውስጥ ቃሉን ቸል ብሎ ኦሮሞ የሚለውን ቃል ይጠቀማል፡፡ እንዲሁም የአለቃ አጥሜና የአለቃ ታዬ ዘመነኛ የሆነው ቦረሊ በመጽሐፉ ኦሮሞ የሚለውን ቃል ሲገለገልበት እናያለን፡፡ ይህ የሚያሳየው ቃሉ ዘመን አመጣሽ ሳይሆን የብሄረሰቡ ቤተሰባዊ መጠርያ ሆኖ ከጥንት የነበረ መሆኑን ነው፡፡
ጌቾ፣ ስለ ጥንታዊው የኦሮሞ ወታደር የጦር ዘይቤ ሲጽፉ ያቀረቡት ፍርድ ከርሳቸው የሚጠበቅ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ እንዲህ ይላሉ፤
“ድንገት ካልተደረሰባቸው በቀር ምንም ቢሆን ከጠላት ጦር ጋራ ፊት ለፊት ውጊያ አይገጥሙም፡፡ የጦር ሀይል መምጣቱን ሲሰሙ በተገኘው አቅጣጫ ሁሉ ይሸሻሉ፡፡ ሲሸሹ ገደል አይመልሳቸውም”
ይህን ፍርድ፣ በጌቾ አእምሮ ውስጥ እንጂ በእውነተኛው ታሪክ ውስጥ አናገኘውም፡፡ የአባ ባህርይ ዘመነኛ የሆኑት የኦሮሞ ተዋጊዎች ስመ-ጥር ጀግኖችና ድል ነሺዎች እንደነበሩ ከጠላት ወገን የሆኑ መንገደኞች ሳይቀር መስክረውላቸዋል፡፡ ለምሳሌ፣ ፓንክረስት በገላውድዮስና በኦሮሞ አስገባሪዎች መካከል የተደረጉ ጦርነቶችን በማስመልከት ቤርድሙዝን ጠቅሶ ሲጽፍ ይህን ይላል
“ስለ ኦሮሞዎች ችሎታና በንጉስ ገላውዲዎስ ላይ የተቀዳጁትን ድል አስመልክቶ ቤርድሙዝ ምስክርነቱን ሰጥቷል፡፡ ከአንድ ውጊያ በኋላ ንጉሱ የረባ ነገር ሳይፈጽም፣ ተረትቶና ደካክሞ ወደ ሰፈሩ ተመለሰ፡፡ ከጥቂት አለፍ ብሎ ቤርድሙዝ፣ ንጉሱ በኦሮሞዎች ተሸንፎ በውርደት ለመሸሽ መገደዱን መዝግቧል›› (The Ethiopian borderlands. ገፅ 284)
(Testimony to the prowess of the Oromo, and some of their victories over Emperor Gelawdewos is given by Berdumus. He records that the Monarch after one battle against the Oromos returned to his camp “wearied and almost defeated without accomplishing anything of value. Not long after this he reports that the Emperor had been defeated by the Oromos..Galawdeos had been obliged to flee “with great indignity”)
ኦሮሞ እንደ ሁሉም የኢትዮጵያ ብሄሮች የጀግንነት ተሰጥኦ እንደታደለ የሚየሳዩ ብዙ ምስክርነቶች አሉ፡፡ ጌቾ እኒህን ምስክርነቶች አይተው እንዳላዩ ሆነው፤ “ካልተደረሰባቸው በቀር ፊትለፊት አይገጥሙም፡፡ ሲሸሹ ገደል አይመልሳቸውም” እያሉ መጻፍ እርሳቸውን ለሚያክል አንጋፋ አረጋዊ ምሁር አይመጥንም እላለሁ፡፡
ጌቾ በቅርቡ በኢንተርኔት ሚድያ ላይ በለጠፉት መጣጥፋቸው “የኦሮሞ ወረራ” ስለሚሉት ሲጽፉ፤ “ከግድያቸው ሰለባቸው ይብስ ነበረ። ባለቅኔው “ጃዊ ቀደደ ሆድ ሆዶሙ ወሰለበሙ እስከ ሕምብርት (ጃዊ ሆድ ሆዳቸውን ቀደደው ሰለባቸው እምብርታቸው ድረስ ሰለባቸው”) ያለው በጎንደር ቤተመንግስት የደረሰውን መቅሰፍት አይቶ ነው፡፡” ብለዋል።
ጌቾ በጎንደር ቤተ-መንግስት ደረሰ የሚሉትን መቅሰፍት ያስረዳልኛል ብለው ይህንን ቅኔ መጥቀሳቸው አስገራሚ ነው፡፡ የቅኔው መነሻ ታሪክ እርሳቸው ከሚሉት እንደሚለይ ማሳሰብ እፈልጋለሁ፡፡ ንጉስ ዳዊት በተባሉ የጎንደር ንጉስ ዘመን በቅባቶችና በደብረሊባኖሶች መካከል የሀይማኖት ውጥረት ነበር፡፡ በአንድ ወቅት ንጉስ ዳዊት ለቅባት ወገኖች አዳልተው፣ እምነታቸውን አልቀበል ብለው አሻፈረኝ ያሉትን የደብረሊባኖስ ባህል ተከታይ ካህናትና ከነ እጨጌያቸው ለመቅጣት ጃዊ የተባለውን ሰራዊታቸውን ላኩባቸው፡፡ የጃዊ ሰራዊት አባላት ካህናቱን ከመግደል አልፈው በመስለባቸው የተደሰተ አንድ የቅባት ባለቅኔ፤
“ሶበ እንቢ ለግዜር ይቤሉ ወእንቢ ለንጉስ ዳዊት
ጃዊ ቀደደ ሆድ ሆዶሙ ወሰለቦሙ እስከሕንብርት” እያለ አላገጠ፡፡ ትርጉሙም፣
“እግዜርንና ንጉስ ዳዊትን እምቢ ባሉ ጊዜ
ጃዊ ሆድ ሆዳቸውን ቀደደው፣ እስከእንብርታቸው ሰለባቸው›› የሚል ነው፡፡
ይህ ሁነት ዳዊት የተባለ የጎንደር ንጉስ በሱ አይን አማጺ ሆነው ያገኛቸውን ዜጎች በግፍ ማስቀጣቱን ከመግለጽ አልፎ የኦሮሞ ወረራን ለማስረዳት የሚጠቀስ ታሪክ አይሆንም፡፡ የጃዊ ጦርም ልክ ዛሬ፣ አጋዚ እንደሚባለው ልዩ ሀይል የቤተ-መንግስት ፈቃድ አስፈጻሚ እንጂ ነጻ ሚና አልነበረውም፡፡
መስለብም ቢሆን የኦሮሞ ብቻ ሳይሆን የትግራይና የአማራ እንዲሁም የከፋ ተወላጅ ወታደሮች ሁሉ ባህሪ ነበር፡፡ ጌቾ፣ በስራዎቻቸው ላይ ደጋግመው በሚጠቅሱት እሸቴ ሐይሉ ባስጻፉት ዜና መዋእል ላይ፣ የአድዋው ራስ ሚካኤል ስኡል ሰራዊት ሰለባ ማቅረቡ ተመዝግቧል፡፡ በወላይታ ዘመቻ የተሳተፈው ፈረንሳዊው መንገደኛ ቫንዳየር፣ ምኒልክ የመስለብ ባህልን በአዋጅ ለማስቀረት ቢሞክሩም እንዳልተሳካላቸው፣ በዘመቻው ላይም አማሮችና ኦሮሞ ወታደሮች በሰለባ መሳተፋቸውን ጽፏል፡፡ ስለዚህ ሰላባን የአንድ ብሄረሰብ ገጽታ ብቻ አድርጎ ማየት ልክ አይደለም፡፡
ፕሮፌሰር ጌታቸው የታሪክ እውነት ሲመሰክሩ እንኳን ሞገደኛ የሆነ የቋንቋ አጠቃቀም ይመርጣሉ፡፡ ይህ አቀራረብ ሰዎች እውነት የሚባለውን ነገር እንዲጠየፉና እንዲፈሩ እንጂ እንዲቀበሉ አያደርጋቸውም፡፡
ለምሳሌ ከላይ በጠቀስኩት መጣጥፋቸው ጌቾ፣ “አጤ ምኒልክና ራስ ጎበና ዳጨ ስፍር ቁጥር በሌለው ጎሳ የተበታተኑትንና የርስ-በርሳቸው የሚባሉትን ኦሮምኛ ተናጋሪዎች አንድ ያደረጉበትን ቀን (የኦሮምኛ ተናጋሪዎች) ማክበር አለባቸው” ይላሉ፡፡ የምኒልክ የማስገበር ጦርነት የማታ የማታ ርስበርስ የተበታተኑት በርስበርስ ወጊያ የሚታመሱትን ጎሳዎች መሀል አንጻራዊ ሰላምና መረጋጋት ማስገኘቱ እውነት ነው፡፡
አፍቃሬ ኦሮሞ የሆነው ደ ሳልቪያክ የኦሮሞ ጎሳዎችን የርስ-በርስ ብጥብጥ ታሪክ በሰፊው ካተተ በኋላ፤ “የኢትዮጵያ ተጻራሪ የሆኑ ዘሮችን ወደ አንድ ትልቅ አገርነት በመለወጥ ንጉሱ (ምኒልክ) አቢሲኒያን ያለ ማቋረጥ ሲያምሳት የነበረውንና የኦሮሞ ጎሳቸዎችን ወንድም በወንድሙ ላይ የሚያስነሳ ትግል እንዲቆም ማድረግ ችለዋል” የሚል ነው፡፡ (By uniting the divided enemies of the Ethiopian races into an all immense nation the Negus has stopped the scourge of feudal wars which endlessly ravaged Abyssinia, and has suffocated the fratricidal struggle of the Oromo tribes) ይላል፡፡
ጌቾ ይህንን ብርቅ እውነት፣ በብሽሽቅ መንፈስ አቅርበው አረከሱት፡፡

No comments:

| Copyright © 2013 Lomiy Blog