መንግሥት የምክክር አድማሱን ያስፋ

ከ400 ሺሕ በላይ አባላት እንዳሉት የሚነገርለት የኢትዮጵያ ሠራተኛ ማኅበራት ኮንፌዴሬሽን (ኢሠማኮ) በቅርቡ ለመንግሥት ያቀረባቸው በርካታ ጥያቄዎች፣ እዚህ አገር ውስጥ ምክክር ምን ያህል አስፈላጊ እንደሆነ ቁልጭ አድርገው የሚያሳዩ ነበሩ፡፡

መንግሥት ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቶ በጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካይነት ከሠራተኛ ማኅበራት ጋር ላደረገው ሰፊ ውይይት ምሥጋና ይገባዋል፡፡ ነገር ግን ይህ ዓይነቱ የምክክር መድረክ በስፋት ተጠናክሮ ከተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ጋር መቀጠል ይኖርበታል፡፡ የግድ ስለሆነ፡፡ 
የሠራተኛ ማኅበራት በሕገ መንግሥት ዋስትና ያገኘው የመደራጀት መብት በስፋት እየተጣሰ መሆኑን በመግለጽ ያቀረቧቸው የዲሞክራሲና የሰብዓዊ መብት ጥያቄዎች በተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎችም የሚነሱ ናቸው፡፡ መንግሥት በተደጋጋሚ የሰብዓዊ መብት ጥሰትና የመልካም አስተዳደር እጦትን በተመለከተ የማሻሻያ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን ቢገልጽም ችግሮቹ ተባብሰው እየቀጠሉ ናቸው፡፡ 

የሠራተኛ ማኅበራቱ ተወካዮች የመደራጀት መብት ምን ያህል ፈተና እንደገጠመው፣ የሥራ ቦታ ደኅንነት የሠራተኞች ፈተና መሆኑን፣ የሠራተኞችም ሆነ የማኅበራት መሪዎች የሥራ ዋስትና በሕገወጥ መንገድ ችግር ውስጥ መግባቱን፣ ፍትሕ ፍለጋ ሲኬድ እንግልት እንደሚገጥም፣ የአገር ውስጥም ሆኑ የውጭ ኩባንያዎች ሕገ መንግሥቱንና ተያያዥ ሕጐችን በመጋፋት ከፍተኛ በደል ሲፈጽሙ ጠያቂ እንደሌላቸው፣ የሠራተኞች ጥቅማ ጥቅምን በድርድር ማስከበር አለመቻሉን፣ የኑሮ ውድነት ጫናና የመሳሰሉ ችግሮችን አንስተዋል፡፡ መንግሥትም መብትን በማስከበር ሽፋን ሕገወጥ ተግባሮች እንደሚፈጸሙ፣ ነገር ግን የሠራተኞች የመደራጀት መብትን ለማክበር በቁርጠኝነት እንደሚሠራ ገልጿል፡፡ ይህ ጥሩ ጅምር ተብሎ ይወሰዳል፡፡  
ከዚህ ባሻገር ግን የሠራተኛ ማኅበራቱ በሚታዩ አሳሳቢ ችግሮች ሳቢያ በኢንዱስትሪው ሰላም ላይ እንቅፋቶች እየተፈጠሩ በመሆናቸው መንግሥት አስቸኳይ ዕርምጃ ይወስድ ዘንድም ጠይቀዋል፡፡ እነዚህ ችግሮች በሠራተኞች ዘንድ ጐልተው የሚታዩ ቢሆንም፣ በአሁኑ ጊዜ በተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ውስጥ የሚያጋጥሙ የዘወትር የምሬት መነሻ ናቸው፡፡ ከወረዳ ጀምሮ እስከላይኛው የመንግሥት መዋቅር ድረስ የመልካም አስተዳደር ፈተናዎች ለሕዝቡ ምሬት ምክንያት ሆነዋል፡፡ የሠራተኛ ማኅበራቱ ተወካዮች ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ያቀረቧቸው ብዙዎቹ ጥያቄዎች መፍትሔ እንደሚያስፈልጋቸው ጥርጥር የሌለው ቢሆንም፣ መንግሥት እያጋጠሙ ያሉ አሳሳቢ ችግሮችን ነቅሶ በማውጣት የሕዝቡን መብት ለማስከበር የምክክር መድረኩን ማስፋት እንዳለበት የማንቂያ ደወል ናቸው፡፡ 
በአሁኑ ጊዜ ሕዝቡ በኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ችግርና አስመራሪ እየሆነ በመጣው የኃይል መቆራረጥ ከፍተኛ እንግልት እየደረሰበት ነው፡፡ ከአንድ ቤተሰብ መኖሪያ ቤት እስከ ከባድ ኢንዱስትሪ ድረስ ይህ የኃይል መቆራረጥ ከፍተኛ የሆነ ኪሳራ እያደረሰ ነው፡፡ የኃይል መቆራረጥ ችግር መንስዔ ምን እንደሆነ በውል የሚያስረዳ አካል የለም፡፡ በተለያዩ ጊዜያት የተለያዩ ምክንያቶች ሲደረደሩ ይሰማል፡፡ ይህ ችግር በአገር ኢኮኖሚ ላይ ሳይቀር ከፍተኛ ኪሳራ እያደረሰ መሆኑን ማንም በቀላሉ ይረዳዋል፡፡ ችግሩን ከሥሩ መንግሎ ለመጣል ከፍተኛ የሆነ የባለሙያዎች ምክክር ያስፈልጋል፡፡ በተለያዩ ተቋማትና በውጭ አገር የሚኖሩ ባለሙያዎችን ከኮርፖሬሽኑ አመራሮችና ባለሙያዎች ጋር በማገናኘት መፍትሔ ለመፈለግ ጥረት ቢደረግ የላቀ ጥቅም ይገኛል፡፡ 
በአዲስ አበባና በክልል ከተሞች የውኃ አቅርቦት መስተጓጐል በነዋሪዎችም ሆነ በአገልግሎት ሰጪ ተቋማትና በፋብሪካዎች ላይ ትልቅ ጉዳት እያደረሰ ነው፡፡ በየቦታው ውኃ ፍለጋ የሚባዝነው ሕዝብ ሥራ እየፈታ ነው፡፡ ሕፃናትን ሳይቀር ችግር ውስጥ እየከተተ ያለው የውኃ አቅርቦት መስተጓጐል ከፍተኛ የምሬት መነሻ እየሆነ ነው፡፡ የተለያዩ ምክንያቶች የሚደረደሩለት የውኃ አቅርቦት መስተጓጐል የባለሙያዎች እገዛና ምክር ካልተደረገለት በጤና ላይ ሳይቀር ትልቅ ጉዳት ያደርሳል፡፡ የውኃ መስመር ሲበላሽ በቶሎ ካልተጠገነ፣ በኃይል እጥረት ምክንያት ውኃ ማሰራጨት አቅቶ ሌላ አማራጭ መጠቀም ካልተቻለ በእርግጥም ይህ ዘርፍ ከፍተኛ የሆነ ችግር አለበት፡፡ መድኃኒቱ ደግሞ በባለሙያዎች የታገዘ የምክክር መድረክ መኖር ነው፡፡ በሚገኘው እገዛ መሠረት ውጤት ማግኘት ይቻላል፡፡ የቴሌኮሙዩኒኬሽን ጉዳይም በዚሁ መሠረት ሊከናወን ይችላል፡፡ በተለይ በኔትወርክ ጥራት ምክንያት የሚታየው ችግር ውስጥ ድረስ ተዘልቆ ካልተፈተሸ ጉዳቱ የአገር መሆኑን ልብ ማለት ብልኅነት ነው፡፡ 
በኮንስትራክሽን፣ በባንክ፣ በወጪና ገቢ ንግድ፣ በገቢዎችና ጉምሩክ፣ በትራንስፖርት፣ በቱሪዝም፣ በኢንዱስትሪ፣ በግብርና፣ ወዘተ ዘርፎች በርካታ ችግሮችን መመርመር ያስፈልጋል፡፡ ችግሮች ተነቅሰው ሲወጡ የዚያኑ ያህል መፍትሔዎቻቸው ከነአማራጮቻቸው ይቀርባሉ፡፡ ችግሮችን የሚያቀርቡ ሁሉ የመፍትሔውም አካል መሆን ይኖርባቸዋል፡፡ ለዚህ ደግሞ የምክክር መድረኮች ያስፈልጋሉ፡፡ ችግሮች ቀርበው መፍትሔዎቻቸው ተጠቁመው ወደ ሥራ ሲገባ የቁጥጥርና የግምገማ መሥፈርቶች መቀመጥ ይኖርባቸዋል፡፡ መንግሥት የምክክር አድማሱን ባሰፋ ቁጥር ለፖሊሲ የሚሆኑ ግብዓቶችን ያገኛል፡፡ በእዚህ መሠረት የሚወጡ ፖሊሲዎች ደግሞ ተቀባይነታቸው ስለሚጨምር የተጀመረውን ዕድገት ለማስቀጠል ይረዳሉ፡፡ 
በአሁኑ ጊዜ በየቦታው በርካታ ብሶቶች ይሰማሉ፡፡ የእነዚህ ብሶቶች መፍትሔ አለማግኘት በሕዝቡ ላይም ሆነ በአገሪቱ ኢኮኖሚ ዕድገት ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ይፈጥራል፡፡ ከወረዳ መስተዳድሮች እስከ ከፍተኛ የመንግሥት አስፈጻሚ አካላት ድረስ ተናቦ ያለመሄድ ችግሮች ስላሉ በየቦታው ብሶቶች ይሰማሉ፡፡ ብሶቶች መፍትሔ ባላገኙ ቁጥር መንግሥት ጫናው ይበረታበታል፡፡ በተለይ በመልካም አስተዳደር እጦት፣ በሰብዓዊ መብት ጥሰት፣ በሙስናና መሰል ተግዳሮቶች ምክንያት ብሶቶች እየገነፈሉ ናቸው፡፡ መንግሥት ይህ ካላሳሰበው ምን ያሳስበዋል? 
የሠራተኛ ማኅበራት ሙስናን የሚያጋልጡ ሠራተኞች ከፍተኛ ችግር እንደሚደርስባቸው ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የገለጹት በምሬት ነው፡፡ የፀረ ሙስና ትግሉ ባለቤት ሕዝብ ነው በሚባልበት አገር ሙስና የሚያጋልጡ ዜጐች ከለላ አያገኙም፣ ይልቁንም የጉዳት ሰለባ እየሆኑ ናቸው ሲባል ከማንም በላይ ሊያመው የሚገባው መንግሥትን ነው፡፡ ለሠራተኞች ጉዳይ በፍርድ ቤቶች የሚሰጠው ትኩረትና የፍትሕ መጓተት አሳሳቢነት የፍትሕ ሥርዓቱ ላይ ጥያቄ ሲያስነሳ መንግሥት ከማንም በፊት ሊሰማው ይገባል፡፡ እነዚህ ሁሉ ችግሮች አሁን ቀረቡ እንጂ ለዓመታት ሲንከባለሉ የመጡ ናቸው፡፡ የምክክር መድረኮች ባለመኖራቸው ግን እንደ አዲስ ይደመጣሉ፡፡ 
በየቦታው በርካታ ችግሮች አሉ፡፡ ችግሮችን አድበስብሶ ማለፍ አደጋ አለው፡፡ ሕዝቡን እያጋጠሙት ያሉት ችግሮች አንድ በአንድ ሊፈተሹ ይገባል፡፡ መፍትሔዎቻቸውም በጋራ መፈለግ አለባቸው፡፡ ስለዚህ መንግሥት ከተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ጋር በመገናኘት ችግሮችን አንጥሮ ያውጣ፡፡ ነጥረው ለወጡ ችግሮችም አስቸኳይ ዕርምጃ ለመውሰድ የምክክር አድማሱ ይስፋ፡፡ ለዚህም መንግሥት በነካ እጁ ምክክሩን በስፋት ያስቀጥል!      
Source: Reporter

No comments:

| Copyright © 2013 Lomiy Blog