የፓን አፍሪካኒዝም ራዕይ ጭንገፋ! (ክፍል ሁለት)





ዚህ በፊት በጻፍሁት ጽሁፍ ስለ ፓን አፍሪካኒዝም ጅማሮ (አመሰራረት) ለማሳየት ሙከራ አድርጊያለሁ። ዛሬ ደግሞ የአፍሪካ ሕብረት እንዴት እንደተመሰረት ትንሽ ካየና በኋላ የፓን አፍሪካኒስቶች ራዕይ እንዴት በአፍሪካ አምባገነን መሪዎች እንደጨነገፈ እናያለን፡፡
    በ1960ዎቹ ብዙ የአፍሪካ ሃገራት ነጻነታቸውን ያገኙበት ነበር፡፡ እነዚህ ነጻነታቸውን የተጎናጸፉ (የተጎናጸፉ የሚለው በምጸት ይነበብልኝ) ሃገራት ዳግም በኢምፔራሊስቶች እንዳይወረሩ የአፍሪካ አንድ መሆንን በየቦታው ማቀንቀን ጀመሩ። በተለይ ኩዋሜ ንኩርማህ አፍሪካ ጠንካራ እንድትሆንና ከውጭ ተጽዕኖ እንድትላቀቅ መዋሃድ አለባት ብሎ ያምን ነበር፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የያኔዎቹ መሪዎቹ ካሁኖቹ ጋር ሲወዳደሩ እጅግ ተራመጅ ነበሩ፡፡ በእነዚህና በሌሎች ምክንያቶች የአፍሪካ አንድነትን (ውህደትን) የሚያቀነቅኑ ቡድኖች አጎነቆሉ። ዋና ዋናዎቹ የሚባሉት ቡድኖች የካዛብላንካና ሞኖረቪያ ናቸው፡፡ ሁለቱም ብድኖች የአፍሪካ አንድነት እንዲመሰረት ጽኑ አቋም ቢኖራቸውም፣ እንዴት ነው መመስረት ያለበት የሚለው ጥያቄ ግን የልዩነታቸው ወሰን ሆኖ
ወደ ንትርክ የገቡበት ጊዜ ነበር። በ1961 የተመሰረተው የካዛብላንካው ቡድን በጋናዊው ኩዋሜ ኑኩርማህ የሚመራ ሲሆን ዓላማቸው አፍሪካ አሁን መዋሃድ (አንድ መሆን) አለባት የሚል ነው። ከነዚህ ቡድኖች መካከል ጊኒ፣ ሊቢያ፣ ግብጽ፣ ሞሮኮ፣ ማሊ፣ አልጄሪያ ይገኙበታል። የሞኖሮቪያው ቡድን ድግሞ በሴኔጋላዊው መሪ ሴንጎር የሚመራ ሲሆን በስሩም ሃያ አራት ሃገራትን፣ ማለትም ናይጄሪያ፣ ሴኔጋል፣ ካሜሮን፣ አይቮሪኮስት፣ ቶጎ፣ ላይቤሪያ እና ሌሎች ብዙ የፈረንሳይ ቅኝ ተገዥ የነበሩ ሃገራትን ያቀፈ ነበር፡፡ የዚህ ቡድን የውህደት መርህ ደግሞ “አፍሪካ መዋሃድ የምትችለው በኢኮኖሚያዊ ትብብር ሆኖ በቀስታ በምታደርገው ጉዘት ነው” ይላሉ፡፡

       ይህንን የሁለቱ ወገኖች ፍጥጫ አርግባ ወደ ውህደት ያመጣቻቸው ኢትዮጵያ ነች፡፡ በተለይ የከተማ ይፍሩ፣ የአጼ ኃይለ ሥላሴ እና የአክሊሉ ሃብተወለድ ሚና ለአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምስረታ የተጫወቱት ሚና አስደማሚና ሁሌም ታሪክ ሲያስታው የሚኖር ጉዳይ ነው፡፡ በሚቀጥለው ጽሁፍ ኢትዮጵያ እና የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን በተመለከተ፣ በተለይም የንኩርማህንና የአጼ ኃይለ ስላሴን ጉዳይ በሰፊው ይዘን እንመጣለን፡፡

     የፓን አፍሪካኒዝም ልጅ የሆነው የያኔው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ሲመረት ዋና ዋና ዓላማዎቹ እነዚህ ነበሩ፣
  1. ቅኝ ገዢዎችን ማስወገድ፣ ያኔ ሁሉም የአፍሪካ ሃገራት ከቅኝ ገዥዎች ስላልተላቀቁ ለምሳሌ እነ ደቡብ አፍሪካ፣ አንጎላ እና ሌሎችም
  2.  በአፍሪካ ሃገራት መካከል አንድነትና ሕብረትን ማበረታታት፣
  3.  ለአፍሪካዊያን ለተሸለ ሕይዎት እና እድገት ለማምጣት
  4. ሉዓላዊነትንና የወሰን አንድነትን ማስጠበቅ
  5.  ሰብዓዊ መብቶችን ማስከበር
  6. በአፍሪካዊያን ሃገራት መካከል የሚካሄዱትን ግጭቶች በሰላማዊና በዲፕሎማሲ መፍታት

ከዚህ በተጨማሪም ሌሎችም ብዙ ዓላማዎችና እቅዶች ነበሩት፡፡ ግን ከተሳኩት ይልቅ ያልተሳኩት ይልቃሉ፡፡ አንዳንዶችም የአፍሪካ ህብረትን የአምባገነኖች ቡድን እንጅ ምን ለውጥ አመጣ ሲሉም ያሄሱታል፡፡ የአፍሪካ ህብረት ከሚነቀፍባቸውና ጥርስ አልባው ድርጅት ያስባሉትን ምክንያቶች ለማየት እንሞክር፡፡

1. ጦርነት፡- አፍሪካን ወደ ኋላ ካስቀሯት አንደኛውና ዋነኛው ምክንያት ጦርነት ነው፡፡ ከሌላው ዓለም በተለየ አፍሪካ ሁሌም ጦርነት ላይ ነች፡፡ የመጀመሪያው ጦርነት ከኢምፔሪያሊስቶች ለመላቀቅ የሚደረግ ጦርነት ነበር፡፡ አሁን ደግሞ አፍሪካ ውስጥ እየተደረገ ያለው ባብዛኛው የእርስ በርስ ጦርነት ነው፡፡ ከዚያ ቀጥሎ ደግሞ በሃገራት መካከል የሚደረገው ጦርነት ነው፡፡ አፍሪካ አሁንም ከነጭ ተጽዕኖ አልወጣችም፡፡ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (የፓን አፍሪካኒስቶች) ራዕይ አፍሪካን ከነጭ ተጽዕኖ ማላቀቅ ነበር፡፡ ነገር ግን ግማሽ ምዕተ ዓመት የሆነው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (የአሁኑ የአፍሪካ ህብረት) ይህን ራዕይ ማሳካት አልቻለም፡፡ አፍሪካን የሚያሽከረክሯት አፍሪካዊያን ሳይሆኑ ኢምፔሪያሊስቶች ናቸው፡፡ አፍሪካ የጦር መሳርያ ሸቀጥ ማራገፊያ ነች፡፡ የአፍሪካ ህብረት በአፍሪካ ሃገራት መካከል የሚፈጠርን ግጭት የመፍታት አቅሙ ደካማ ነው፡፡ ከዚያ ይልቅ ኢምፔሪያሊስቶች ባህር ተሻግረው በመምጣት ያልተመቻቸውን ዙፋን እየነቀነቁ የራሳቸውን አሻንጉሊት ይጎልታሉ፡፡ ካልሆነም አገሪቱን አተረማምሰዋት ይሄዳሉ፡፡ በቅርብ በሊቢያ የሆነውን ማሰብ በቂ ይመስለኛል፡፡ የአፍሪካ ህብረት በ1963 ያረቀቀውን ቻርተር መተግበር አቅቶት በሚሊዮን የሚቆጠሩት አፍሪካዊያን ሞተዋል፣ ተሰደዋል፣ ተርበዋል፡፡ የበፊቱን ትተን በ21ኛው ክፍለ ዘመን ብቻ በአፍሪካ የተካሄዱትን እና እየተካሄዱ ያሉትን የርስ በርስ ጦርነትና ግጭቶች ብቻ ትንሽ ለማየት እንሞክር፡፡

የሶማሊያ፣ የሱዳን፣ የሴንትራል አፍሪካ ሪፐብሊክ፣ የአይቮሪኮስት፣ የቻድና የሊቢያ የእርስ በርስ ጦርነቶች፣ የኒጀር ዴልታ፣ የኪቩ፣ የኤርትራ-ጅቡቲ ግጭቶች ወዘተ መጥቀስ ይቻላል፡፡ በአሁኑ ሰዓት ደግሞ የማሊ፣ የናይጀሪያ፣ የሰሜን እና ደቡብ ሱዳን፣ የሶማሊያ፣ የሴንትራል አፍሪካ ሪፐብሊክ እና ሌሎችም ጉዳይ ለአፍሪካዊያን የራስ ምታት ሆነዋል፡፡ በሌሎች የአፍሪካ ሃገራትም የጎሳ ግጭቶችና የርስ በርስ ጦርነቶች እንደተጎበጎቡ ናቸው፡፡ የአፍሪካ ህብረት (አንድነት) ጥንካሬው ተደርጎ የሚወሰደው ቅኝ ገዥዎችን ከአፍሪካ ለማስወጣት ያደረገው ትግል እና አሁን ደግሞ በትንሹ በሶማሊያና መሰል አገሮች የሚወስደው የማረጋጋት ተግባር እንደሆነ ብዙዎች ያምናሉ፡፡

2. ዲሞክራሲ፡- አብዛኛው የአፍሪካ ሃገራት ዲሞክራሲን ስሙ ሲጠራ እንጂ በተግባር አያውቁትም፡፡ ከነጻነት ማግስት የመጡት የአፍሪካ መራሂያን አፍሪካን የዲሞክራሲ ባለቤት እናደርጋለን ብለው ቢነሱም ስልጣናቸውን በወታደሮች እየተነጠቁ ወደ እስር ቤት ተወርውረዋል፡፡ ተገድለዋል፡፡ ሌሎችም የስልጣን ወንበር ሞቋቸው የሚቀናቀናቸውን እያሰሩና እየገደሉ ብዙ ዓመት የገዙ አሉ፡፡ ምንም እንኳ ዓለም 21ኛው ክፍለ ዘመን ገብቻለሁ ብላ ብታቅራራ፣ አፍሪካ ግን ዘመነ ኦሪት ላይ ነኝ እያለች ነው፡፡ በጣት ከሚቆጠሩ ሃገራት በስተቀር ዲሞክራሲን ከተሰቀለችት ቆጥ ማውረድ አቅቶን ዘላለም አንጋጠን እያነባን ነው፡፡ እናም የአፍሪካ አንድነት ድርጅት በ1963 ሲመሰረት አፍሪካዊያንን በዲሞከራሲ ብርሃን አጎናጽፋለሁ ብሎ በቻርተሩ ፈርሞ ቢያጸድቀውም፣ እኛ ብዙ የአፍሪካ ሃገራት ግን እንኳን የዲሞክራሲን ብርሃን ልንጎናጸፍ ቀርቶ ብርሃኑ በየት እንደበራ አላየነውም፡፡ እስካሁንም ጨለማ ውስጥ ነን፡፡ የአፍሪካ መሪዎችም በየዓመቱ ከመሰብሰብ ውጭ ይሄ ነው የሚባል ተጨባጭ የዲሞክራሲ መሰረት ግንባታ ላይ ሲወያዩና ሲተገብሩ አላየናቸውም፡፡ እኛ የምናያቸው እና የምንሰማው እንዲህ እናደርጋለን ብለው ሲፎክሩና በወይን ሲቻረሱ ነው፡፡

3. ረሃብ፡- አፍሪካ እስካሁን ራሷን መመገብ አልቻለችም፡፡ እስከ አሁንም ረሃብ በብዙ ሃገሮች እንደተጋረጠ ነው፡፡ በጥቅምተ 10/ 2012 አልጄዝራ ይዞት የወጣው ሪፖርት፣ 75% የሚሆነው የአፍሪካ ህዝብ በልቶ የማደር ዋስትናቸው አደጋ ውስጥ እንዳለ ነበር Maplecroft’s Food Security Risk Index በመነሻ በማድረግ የገለጸው፡፡ በቅርቡም ኦክስፋም እንደገለጸው በምዕራብ አፍሪካ ሃገሮች ቻድ፣ ኒጀር፣ ሴኔጋልና ማሊ በ2012 ሙሉ ዓመቱን 18 ሚሊዮን ህዝብ በረሃብ አለንጋ ሲገረፍ ነው የከረመው፡፡ በምስራቅ አፍሪካም ኢትዮጵያ፣ ኬንያ፣ እና ሶማሊም ሁሌ የረሃብ ነገር እንዳገረሸ ነው፡፡

የአፍሪካ ህብረት አንደኛው ዓላማቸው አፍሪካዊያን የተደላደለ ኑሮ እንዲኖሩ ማደረግ ነበር፡፡ ግን አልቻሉም፡፡ መሪዎቹ ህዝባቸው ተርቦ እያደረ እነሱ ግን የተንደላቀቀ ኑሮ ይኖራሉ፡፡ ምን መኖር ብቻ ቱጃር ከመሆንስ ማን ያግዳቸዋል? ህዝባቸው ከሃገር ሃገር ሆዱን ሞልቶ ለማደር እየተንከራተተ ነው፡፡ ገሚሱም ከሃገር ለመውጣት በሚያደርገው ጥረት መንገድ ላይ ይሞታል፡፡ ትረፍ ያለው ደግሞ ቢያንስ ወደ እስር ቤት ይወረወራል፡፡ ምንም ጠያቂ ባይኖረው የእስር ቤቱ ጠባቂዎች በረሃብ አለንጋ እና በዱላ ዘወትር ይጠይቁታል፡፡ ስንቶችስ በሌባ ተዘረፉ? ስንቶችስ ተደፈሩ? የአፍሪካ ህብረት ሲነሳ ትዝ የሚለኝ የአውሮፓ ህብረት ነው፡፡ አውሮፓ በርግጥም የተባበረች ነች፡፡ እኛ አፍሪካዊያን ግን እንደ አውሮፓዊያን ለመተባበር በያዝነው ፍጥነት ከመቶ አመት በላይ ሳይጨርስብን አይቀርም፡፡ አውሮፓ ውስጥ አንድ ግለስብ የትም ሃገር ሂዶ የመኖርና የመስራት መብት አለው፡፡ አፍሪካ ውስጥ ግን ያለ ፍቃድ የትም ብትገኝ እስር ቤት ነህ፡፡ ያውም ከስንት ስቃይ ጋር፡፡ ስለዚህ የአፍሪካ ህብረት ምግባሩና ስሙ አይገናኝም፡፡

4. ኢኮኖሚ፡- አፍሪካ አሁንም ለኢምፔሪያሊስቶች ጥገኛ ነች፡፡ ኢኮኖሚዋ የሚሾረው በራሷ ፈቃድ ሳይሆን በምዕራባዊያን ይሁንታ ነው፡፡ ሁሌ ተበዳሪ ነች፡፡ ለብድሯ የምትከፍለው ወለድ ራስ የሚያዞር ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ልጆቿ ተጠቃሚ ሳይሆኑ ሃብቷ በአምባገነን መሪዎቿ ደጋፊነት እየተዘረፈ ወደ ውጭ ሃገር ይሄዳል፡፡

እናም የፓን አፍሪካን ራዕይ የሆነውና የአፍሪካ አንድነት ድርጅት በቻርተሩ ያጸደቀው አፍሪካን አንድ (የተባበረች) የማድረጉ፣ በኢኮኖሚ የመዋሃዱ፣ የነጭ ተጽዕኖን አሽቀንጥሮ የመጣሉ፣ ራስን መመገብ መቻል፣ በዲሚክራሲ ስርዓት ግንባታ የተጓዘው ጉዞ የሚያሳፍርና አሳዛኝ ነው፡፡ አምባገነን መሪዎችም ማድረግ እየቻሉ ለራሳቸው ጥቅም ብቻ በመቆማቸው የፓን አፍሪካኒስቶችን ራዕይ አጨነገፉት፡፡

No comments:

| Copyright © 2013 Lomiy Blog